ምዕራፍ ሁለት
ቁ. 9-10 ‘‘በብርሃን ውስጥ አለሁ የሚል ወንድሙን የሚጠላ ገና እስካሁን በጨለማ ውስጥ አለ፡፡ ወንድሙን የሚወድ
ግን በብርሃን ይኖራል’’ የክርስትና ሃይማኖት ማሰሪያው ፍቅር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሰራ
እምነት እንጂ መገረዝ ወይም አለመገረዝ አይጠቅምም (ገላ. 5፡6) እንዳለ ወንድምን መውደድ አንድ ሰው በብርሃን ስለመኖሩ ማረጋገጫ
ሆኗል፡፡ ወንድሙን የሚጠላ ከእግዚአብሔር ሊሆን አይችልምና፡፡
በጎ ምግባራት በመዳን ሕይወት ውስጥ ታላቅ ድርሻ አላቸው፡፡ በብርሃን
እንድንሆንና ከእግዚአብሔር ጋር ህብረት እንዲኖረን ወንድሞቻችንንና እህቶቻችንን ልንወድ ያስፈልገናል፡፡ ወንድሞቻችንን እየጠላን
በብርሃን ልንሆንና ከእግዚአብሔርም ጋር ህብረት ሊኖረን አይችልም፡፡ ወንድሞቻችንን ስንወድ ግን ከጨለማ ሥራ ስለምንለይ በብርሃን
መሆን ይቻለናል፤ በዚህም ደግሞ ከአምላካችን ከእግዚአብሔር ጋር ህብረትና አንድነት ይኖረናል፡፡
‘‘በዚህም የእግዚአብሔር ልጆችና የሰይጣን ልጆች ይታወቃሉ፤ ጽድቅንም የማይሠራ ሁሉ ከእግዚአብሔር የተወለደ አይደለም፤
ወንድሙንም የማይወድ እንዲሁ ነው፡፡’’ 1ኛ ዮሐ 3፣10፡፡ ጽድቅ በእምነት ብቻ ሳይሆን በጎውን በማድረግና በመሥራትም ነው፡፡ ጽድቅን
የማያደርግና ወንድሙን የማይወድ ሁሉ የሰይጣን ልጅ ነው፤ በእግዚአብሔር ማመኑ ብቻውን የእግዚአብሔር ልጅ ሊያደረገው አይችልምና፡፡
አጋንንትም ያምናሉ ይንቀጠቀጡማል ነገር ግን የእግዚአብሔር ልጆች አይባሉም (ያዕ 2፡19)፡፡ ጽድቅ በጎውን በማድረግና ወንድሞቻችንን
በመውደድ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይነገረናል፡፡ ክርስትና የማድረግ ሕይወት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፉልን ብዙዎቹ ትምህርቶች
በተግባር የምንታዘዛቸው ናቸው፡፡ እነዚህም ደግሞ ባነበብናቸው ቁጥር ጽድቅን ማድረግ ስለሚያስችሉን ጽድቅን በመሥራት የእግዚአብሔር
ልጆች መሆን እንደምንችል ይነግሩናል፡፡ ጌታችን በወንጌል ‘‘እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው።’’ እንዳለን ቃሉ
መንፈስም ነውና በሕይወታችን ውስጥ ይሠራል፤ በጎ ማድረግንም ያስተምረናል፡፡ ዮሐ 6፣63፡፡ ‘‘ከአፌ የሚወጣ ቃሌ እንዲሁ ይሆናል፤
የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም፡፡’’ እንዲል ቃሉን ስናምንና ልንታዘዘው ስንፈቅድ
ብቻ በእኛ ውስጥ ይሠራል፤ በዚህም ጊዜ በሥራ የሚገለጥና የሚታይ እምነት ይኖረናል፡፡ ኢሳ 55፣11፡፡
ቁ. 28-29 ‘‘አሁንም ልጆቼ ሆይ፣ በሚገለጥበት ጊዜ መወደድን እናገኝ ዘንድ፣ በሚመጣበትም ጊዜ ከእርሱ የተነሳ
እናዳናፍር በእርሱ ጸንታችሁ ኑሩ፡፡ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ብታውቁ ጽድቅን የሚያደርግ ሁሉ ከእርሱ እንደተወለደ እወቁ፡፡’’ በእርግጥ መጽሐፍ ቅዱስ ለተቀበሉትና
በስሙ ለሚያምኑት ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን እንደሰጣቸው ይነግረናል፡፡ ዮሐ 1፣12፡፡ በእምነት ብቻ ሳይሆን
ጽድቅን/በጎ ምግባራትን በማድረግም ከእግዚአብሔር እንደምንወለድና የእግዚአብሔር ልጆች እንደምንሆንም ደግሞ ይነግረናል፡፡ ጽድቅን
የማያደረግ ሁሉ ከእግዚአብሔር አልተወለደምና፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ስለምን ይሆን እዚህ ላይ ስለእምነት ሳያነሳ ጽድቅን ስለማድረግ ብቻ
የጻፈልን? ምክንያቱም በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን ባሻገር እርሱ እንደተመላለሰ እኛም ደግሞ በጽድቅ መመላለስና
ጽድቅን ማድረግ ስለሚያስፈልገንም ነው፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጻድቅ መሆኑን የማወቃችን ጥቅሙ ጽድቅን ለማድረግ
ነው፡፡ ‘‘ለዚህ ተጠርታችኋልና፤
ክርስቶስም እኮ ፍለጋውን ትከተሉ ዘንድ ምሳሌውን ሊተውላችሁ ስለእናንተ መከራን ተቀብሏል፡፡’’ 1ኛ ጴጥ 2፣21፡፡
ክርስትና ይህ ነው በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ብቻ ሳይሆን የእርሱን ፍለጋም መከተል፡፡ ስላመንን ብቻ እንድናለን
ብለን ፍለጋውን ከመከተል ፈቀቅ ብንል ልንድን አንችልም፡፡ የምንከተለው ፍለጋ ደግሞ እርሱ በምድር ላይ እንደተመላለሰና እንዳሳየን
በጽድቅ ሕይወትና ከኀጢአት በመራቅ የሚደረግ መመላለስ ነው፡፡ በክርስቶስ ማመኑን ወድደን ክርስቶስ የኖረውን የተቀደሰ ሕይወት ልንተውና
ልንጥል አይቻለንም፡፡ የትኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ይህን አይደግፍም፡፡ በክርስቶስ ካመንን በኋላ እርሱ ጾሞ እንዳሳየን አንዲሁ
ደግሞ እንጾማለን፣ መጸለይን እንዳሳየን እንዲሁ እኛ ደግሞ እንጸልያለን፣
በገዳመ ቆሮንቶስና በጌቴ ሴማኒ የአትክልት ስፍራ በመንፈሳዊ ተጋድሎ (በጸሎት፣ በሰጊድና በቁመት) መቆየትን እንዳስተማረን
እንዲሁ እኛ ደግሞ እናደርጋለን፡፡ መቼም ክርስቶስ የጾመውና የጸለየው ለኃጢአታችን ሥርየት ነው ካላልን በቀር፡፡ የኃጢአታችን ስርየትማ
በደሙ መፍሰስ ብቻ ነው የተደረገው፤ መጾሙና መጸለዩ ግን እኛ እንጾምና እንጸልይ ዘንድ አርአያ ሊሆንልን ነው፡፡ በደሙ ከሆነልን ሥርየት የተነሳ የምንኖረው
አዲስ ሕይወት የምንጠብቀውና ወደ ክርስቶስ የምናድግበት፤ ወደ ክብሩም ሙላት የምንደረስበት መንገድ ሲሆን ይኽውም ክርስቲያናዊው
ምግባር፣ የተቀደሰውና በድርጊት የተገለጠው ኑሯችን ነው፡፡ እርሱ እንዳደረገ ስናደርግና እርሱ እንደተመላለሰ መመላለስ ስንችል ያን
ጊዜ ወደ ክርስቶስ እንደርሳለን፤ ወደ መዳንም እንገባለን፡፡