ምዕራፍ ሦስት
ቁ. 6-8 ‘‘በእርሱም የሚኖር ሁሉ አይበድልም፣ የሚበድልም ሰው አያየውም፣ አያውቀውምና፡፡ ልጆቼ ሆይ
ማንም አያስታችሁ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ሁሉ ጻድቅ ነው፡፡ ኀጢአትን የሚሠራትም ከሰይጣን ወገን ነው፡፡’’ በክርስቶስ የሚኖሩ ሁሉ በደልን
አያደርጉም፣ መበደላቸው ከክርስቶስ እንደሚያርቃቸው ያውቃሉና፡፡ የተጠራነው በክርስቶስ እንድናምን ብቻ ሳይሆን ካመንን በኋላ እንዳንበድል፣
በጥንቃቄ እንድንኖርም ጭምር ነው፡፡ ብንበድል እንኳን ኀጢአታችንን በንስሓ ልናርቅ ያስፈልገናል፡፡ የክርስትና ትክክለኛው አስተምህሮ
ማመን ብቻ ሳይሆን፣ ካመኑ በኋላ አለመበደልንና ጽድቅን ማድረግንም ይጨምራል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ‘‘የሚበድልም ሰው አያየውም’’ ሲል የጻፈልን ለምን
ይሆን? እዚህስ ጋር ስለምን ስለ እምነት ሳይጽፍልን ቀረ? መጠራታችን በስሙ እንድናምን ብቻ ሳይሆን ስለስሙ ኀጢአትን ማድረግን
ትተን ጽድቅን ማድረግን እንድንለማመድም ጭምር ነው፡፡ ስላመንን ብቻ ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግባትና እርሱንም ማየት አንችልም፡፡
ከመበደልና ክፉውን ከማድረግ ራሳችንን ማራቅ ይጠበቅብናል፡፡ በእርግጥ በእምነት እግዚአብሔርን ማየት ይቻላል፤ በእምነት ብቻ ግን
አይደለም በበጎ ምግባራትም ጭምር እንጂ፡፡ በክርስቶስ የሚያምን ሰው ክርስቶስ እንደተመላለሰበት ባለ መመላለስ፣ በተቀደሰ ሕይወትና
በበጎ ምግባራት ሊመላለስ ያስፈልገዋል፡፡ ‘‘እግዚአብሔርንም የሚያምኑት በመልካም ሥራ፤ በጥንቃቄ እንዲጸኑ፣ እነዚህን አጽንተህ እንድትናገር
እፈቅዳለሁ’’ ቲቶ 3፣8 ተብሎ የተጻፈልን
በመልካም ሥራ መጽናት በመዳን ሕይወት ውስጥ ትልቅ ድርሻ ስላለው ነው፡፡ በመልካም ሥራ ለመጽናት መጠንቀቅና መትጋት ካልቻልን ግን
እምነታችን ብቻውን እግዚአብሔርን ደስ ሊያሰኘውና ወደ መዳንም ሊያደርሰን እንደማይችል ከመጽሐፍ ቅዱስ እናነባለን፡፡
‘‘በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል፡፡’’ 1ኛ ዮሐ 2፣6፡፡ ክርስትና በክርስቶስ ማመን ብቻ ሳይሆን ክርስቶስ እንደተመላለሰ መመላለስም
ደግሞ ነው፡፡ በክርስትና ሕይወት ውስጥ በክርስቶስ ማመን የሚያስፈልገውን ያህል ክርስቶስ እንደተመላለሰ መመላለስም እንዲሁ ያስፈልጋል፡፡
እምነት ብቻውን ከሌሎች ክርስቲያናዊ ተግባራት እንደሚበልጥና ለመዳን የሚያስፈልግ ብቸኛ ነገር መሆኑን ግን በየትኛውም የመጽሐፍ
ቅዱስ ክፍል ውስጥ አናገኝም፡፡ ‘‘ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው፥ እግዚአብሔርን ያዩታልና፡፡’’ ማቴ 5፣8 እንደተባለ
እግዚአብሔርን የምናየው ደግሞ ከዚህ ምድር ይልቅ በመንግሥቱ ነው፤ ይህ ከሆነ ታዲያ ለምን በእርሱ የሚያምኑ ተብሎ አልተጻፈም?
በእርግጥ ሳናምን ልናየው አንችልም፤ ስላመንንም ብቻ ደግሞ አናየውም፡፡ ስለሆነም እግዚአብሔርን በመንግሥቱ የሚያዩት የሚያምኑ ብቻ
ሳይሆኑ በእርሱ ባላቸው እምነት የተነሳ ሰውነታቸውን/ሕይወታቸውን ከኀጢአትና ከፍትወታት እኩያት ንጹህ ያደረጉት ናቸው፡፡ ክርስትናን
የተማርነው እንዲህ ነው፡- አንዱን ይዘን ሌላውን ደግሞ ትተን ሳይሆን ሁሉንም ማድረግንና መታዘዝንም ነው፡፡ በእምነት እንደምንጸደቅ
መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፣ በእምነት ብቻ እንደምንጸድቅ ግን አይነግረንም፡፡ በበጎ ምግባራት/ጽድቅን በማድረግ አንደምንጸድቅም ይነግረናል፤
በበጎ ምግባራት/ጽድቅን በማድረግ ብቻ እንደምንጸድቅ ግን አይነግረንም፡፡ ‘‘ልጆቼሆይ ማንም አያስታችሁ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ
ሁሉ ጻድቅ ነው፡፡’’ተብሎ እንደተጻፈ እውነተኛው ክርስትና እንግዲህ ይህ ነው፡- እንድናምንም፣ በጎ ምግባራትንም
እንድናደርግ የሚነግረን! ‘‘መዳን በእምነት ብቻ፣ መዳን በጸጋው ብቻ፣ መዳን በበጎ ምግባራት ብቻ’’ የሚለው አስተምህሮ ከመጽሐፍ
ቅዱስ ያፈነገጠ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን በእምነት፣ በጸጋውና በበጎ ምግባራት ስለመዳን ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ አብረው እንደሚሄዱና
እንደሚደጋገፉ እንጂ እንደሚቀዋወሙ አይነግረንም፡፡
ቁ. 10 ‘‘ በዚህም የእግዚአብሔር ልጆችና የሰይጣን ልጆች ይታወቃሉ፤ ጽድቅንም የማይሠራ ሁሉ ከእግዚአብሔር
የተወለደ አይደለም፤ ወንድሙንም የማይወድ እንዲሁ ነው፡፡’’ በእርግጥ የእግዚአብሔር ልጆች ከምንሆንበት
መንገድ አንዱ እምነት ነው፡፡ ‘‘ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡’’ ተብሎ ተጽፏልና፡፡
ዮሐ 1፣12፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስን መቀበልና በስሙ ማመን የእግዚአብሔር ልጆች መሆን የሚቻልበትን ሥልጣን ይሰጣል፡፡ ሆኖም ግን
እርሱን መቀበላችንና ማመናችን ብቻውን የእግዚአብሔር ልጆች አያደርገንም፤ ስለሆነም ጽድቅን የሚሠራና ወንድሙን የሚወድም እንዲሁ
የእግዚአብሔር ልጅ ይሆናል፡፡ ‘‘ጽድቅንም የማይሠራ ሁሉ ከእግዚአብሔር የተወለደ አይደለም’’ እንዲል ከእግዚአብሔር
የምንወለደው ክርስቶስ ኢየሱስን በመቀበልና በስሙ በማመን ብቻ ሳይሆን ጽድቅንና በጎውን ሁሉ በመስራትም ነው፡፡ ‘‘እንግዲህ በጎ ለማድረግ
አውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነው፡፡’’ ተብሎ እንደተጻፈ ኃጢአት ክፉውን ማድረግ ብቻ ሳይሆን በጎውን ለማድረግ እያወቁ
ማድረግ አለመቻል/ላወቁት ቃሉ አለመታዘዝም ነው፡፡ ኃጢአተኞች ደግሞ የእግዚአብሔርን መንግስት ሊወርሱ አይችሉም፡፡ ያዕ 4፣17፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጆች የምንሆነው በክርስቶስ ኢየሱስ በማመንና እርሱንም በመቀበል እንደሆነ ይነግረናል፤ እንዲሁ ደግሞ
ጽድቅን በመሥራትና ሰዎችን በመውደድም የእግዚአብሔር ልጆች እንደምንሆንም ይነግረናል፡፡ እናም ሁለቱንም አንቀበላለን፣ በሁለቱም
እንጸናለን እንጂ አንዱን ተቀብለን ሌላኛውን አንተውም፣ አንዱን የእግዚአብሔር ቃል ከሌላኛው አናስበልጥም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን
መዳን በእምነት፣ በጸጋና በበጎ ምግባራት እንደሆነ ነው፤ ስለሆነም ሦስቱንም እኩል እናምናለን፣ እንቀበላለንም እንጂ ከሦስቱ አንዱን
ወይም ሁለቱን ብቻ ነጥለን አንወስድም፡፡
ይቀጥላል . . .
ይትባረክ እግዚአብሔር አምላከ አበዊነ!