Tuesday, January 31, 2017

መጀመሪያይቱ የቅዱስ ዮሐንስ መልዕክት ምዕራፍ አራት



መጀመሪያይቱ የቅዱስ ዮሐንስ መልዕክት ምዕራፍ አራት
(መዳንና በጎ ምግባራት በመጀመሪያይቱ የቅዱስ ዮሐንስ መልዕክት)
ቁ. 4 ልጆች ሆይ እናንተ ግን ከእግዚአብሔር ናችሁ፣ ክፉውንም አሸንፋችሁታል፡፡ ከእግዚአብሔር የሆኑ ሁሉ ክፉውን ያሸንፋሉ፤ ክፉውን ማሸነፍ የምንከተለው የክርስቶስ ፍለጋ ነውና፡፡ በዓለም ግን መከራን ትቀበላላችሁ፤ ነገር ግን ጽኑ፤ እኔ ዓለሙን ድል ነስቼዋለሁና፡፡ ዮሐ 16፣33፡፡ ተብሎ እንደተጻፈ ጽኑ የተባልንበት ይህ መጽናት እንዴት ያለ ነው? መጠራታችን ክርስቶስ ለኖረው ሕይወት ነው፣ የክርስቶስ ሕይወቱ ደግሞ በዘመነ ሥጋዌው በምድር ላይ የተመላለሰው የተቀደሰ መመላለሱ ነው፡፡ እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርኹኽ ዮሐ 17፣4 ተብሎ እንደተጻፈ የክርስቶስን ፍለጋ እንከተላለን ስንል እርሱ የአባቱን ፈቃድ እንደፈጸመ እኛም እስከሞት የወደደንን የአምላካችንን ፈቃድ እንከተላለን እንፈጽማለንም ማለታችን ነው፡፡ ከእርሱ ፈቃድ የተለየ ፈቃድ ካለን እንዴት የእርሱ ልንሆን እንችላለን? መጠራታችን በስሙ ልናምን ብቻ ሳይሆን በስሙ መከራንም ልንቀበል ነውና ክርስትና በስሙ ማመን ብቻ ሳይሆን በስሙ መጋደልና መከራ መቀበልም ነው፡፡ ፊልጵ 1፣29፡፡ ስለሆነም እውነተኛው የክርስትና አስተምህሮ በክርስቶስ ስም ስለማመን እንደሚያስተምረው ሁሉ ለክርስቶስ መኖርን፣ ለእርሱ ብሎ ማድረግንና መጋደልንም ያስተምራል፡፡
የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን እንከተለው እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሶ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጧልና፡፡ በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን እስኪ አስቡት፡፡ ገና አልጸናችሁምና፣ ደማችሁን ለማፍሰስ እስክትደርሱ ኀጢአትን ተጋደሏት፣ አሸንፏትም፡፡ ዕብ 12፣2-4፡፡ ክርስቶስ የናቀው ነውር ምንድን ነው? በጎውን ማድረግ የመዳን መንገድ ባይሆን ኖሮ ክርስቶስ በምድር ላይ ለሠላሳ ሦስት ዓመታት መመላለስ ሳያስፈልገው ደሙን ብቻ ሊያፈስልን ይቻለው ነበር፡፡ በእነዚህ ሁሉ አመታት ግን ያሳየንና የተወልን የምንከተለው ፍለጋ አለን፡፡ ክርስትና በክርስቶስ ደም፣ በቤዛነቱ ማመን እንደሆነ ሁሉ የክርስቶስ ፍለጋውን መከተልም ነው፡፡ በክርስቶስ ባለን እምነት ለማደግ የምንተጋውን ያህል እንዲሁ ደግሞ ፍለጋውን ለመከተልና በተግባር የተፈተነውን ክርስትና ለመኖርና ለማድረግም እንተጋለን፤ በክርስቶስ እናምናለን የምንል ከሆነ የእምነታችን ራስና ፈጻሚ የሆነውን እርሱን መከተልና እርሱ እንደተመላለሰም ልንመላለስ ያስፈልገናልና፡፡
እንመላለስበት እግዚአብሔር አስቀድሞ ላዘጋጀው በጎ ሥራ በኢየሱስ ክርስቶስ የፈጠረን ፍጥረቱ ነንና፡፡ ኤፌ 2፣10፡፡እንግዲህ ምን እንላለን? እግዚአብሔር የፈጠረን በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ እንድናምን ብቻ ሳይሆን እንመላለስበት ዘንድ አስቀድሞ ላዘጋጀው በጎ ሥራውም ጭምር ስለሆነ በስሙ እንደምናምን ሁሉ ስለ ስሙ ብለን በጎውን ማድረግና በተቀደሱ ተግባራት መመላለስንም አንተውም፡፡ ይህን ብቻ አድረጉ (እምነትን ብቻ) የሚል የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የለምና! እውነተኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የሚነግረንና የሚያስተምረን በበጎ ሥራ ሁሉ ፍሬ እያፈራችሁ፣ እግዚአብሔርንም በማወቅ እያደጋችሁ በሁሉ ደስ ታሰኙት ዘንድ፡፡ በፍጹም ኃይል፣ በክብሩ ጽናት፣ በፍጹም ትዕግስት፣ በተስፋና በደስታም ጸንታችሁ፡፡ ብሎ ነው፡፡ ቆላ 1፣10-11፡፡ በእምነት እንድንጸና፣ በክርስቶስ ላይ ባለን እምነት እንድንደገፍ እንደሚነግረን ሁሉ በበጎ ሥራ፣ በፍጹም ትዕግስትና በተስፋ እንድንጸናም ይነግረናል፡፡ በፍጹም ትዕግስት የተባልነው ክርስትና አንድ ጊዜ አምነን የምንተወው ብቻ ሳይሆን በእምነታችን ውስጥ የምንታዘዘው በድርጊት የሚገለጥ ሕይወትና የምንታገሰው መከራም ጭምር ስለሆነ ነው፡፡
ቁ. 7-8 ወንድሞቻችን ሆይ እርስበርሳችን እንፋቀር፤ ፍቅር እግዚአብሔር ነውና፤ የሚፋቀርም ሁሉ እርሱ ከእግዚአብሔር ተወለደ፤ እግዚአብሔርንም ያውቀዋል፡፡ ወንድሙን የማያፈቅር እግዚአብሔርን አያውቅም፤ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና፡፡ክርስትና እምነት ብቻ ሳይሆን በእምነት ውስጥ የሚሆን በተግባር የሚገለጥ በጎ ምግባርም ነውና በእምነት የእግዚአብሔር ልጆች ሆነን እንደምንወለደው ሁሉ በበጎ ምግባራትና በተቀደሰ ክርስቲያናዊ ኑሯችንም ከእግዚአብሔር እንወለዳለን፡፡   በዮሐንስ ወንጌል ላይ ደግሞ እንዲህ ተጽፏል፡- ለተቀበሉት ሁሉ በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡ ዮሐ 1፣12፡፡ በእምነታችን የእግዚአብሔር ልጆች እንደምንሆን ሁሉ በበጎ ምግባራችንም የእግዚአብሔር ልጆች እንሆናለን፡፡ ስለሆነም በክርስትናችን ውስጥ ለበጎ ምግባራት ያለን ቦታ ለእምነት ከሚኖረን ቦታ እንዲያንስ አንፈቅድም፡፡ በእምነት ለማደግ የምንተጋውን ያህል በበጎ ምግባራት ለማደግም እንዲሁ ደግሞ በእጅጉ እንተጋለን፡፡ ከቅዱስ መጽሐፍና ከቅዱሳን አባቶቻችን እንዲህ ተምረናልና! ግን እላችኋለሁ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ የሚረግሟችሁን መርቁ፣ ለሚጠሏችሁ መልካም አድርጉ፤ ስለሚበድሏችሁና ስለሚያሳድዷችሁም ጸልዩ፡፡ በሰማያት ላለው አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ፡፡ ማቴ 5፣44-45፡፡ ይህ ከሆነ የእግዚአብሔር ልጆች የምንሆነው በእምነታችን ብቻ ሳይሆን በበጎ ምግባራችንም ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህም በእምነታችን ብቻ ወይም በበጎ ምግባራችንም ብቻ አንድንም ማለት ነው፡፡ ታዲያ እውነተኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የትኛው ነው?
እውነተኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ስለመዳን የሚነግረን መዳናችንን እግዚአብሔር በራሱ በነጻ እንደሰጠን ይህም ደግሞ ጸጋው እንደሆነ፤ ይህም በነጻ የሆነልንን ጸጋውን ደግሞ ልናምን እንደሚያስፈልገን ነው፡፡ ጸጋው በዓለሙ ሁሉ በሙላት መሆኑና መደረጉ ብቻውን ዓለሙ ይህንን ጸጋ እስካላመነና እስካልተቀበለ ድረስ ሊድን አይቻለውምና ይህንን ጸጋ ማመን ያስፈልጋል፡፡ በዚህ ጸጋ ከታመንን በኋለ ደግሞ እንዳመንን እንዲሁ ደግሞ ጸጋውን በሥራችን የምንታዘዝ ልንሆን ያስፈልገናል፡፡ ጸጋው በእምነት አድኖናል ብለን በጎውን ከማድረግ ብንሰንፍ ጸጋው ብቻውን ሊያድነን አይችልምና፡፡ ወንድሞቻችን አሁንም በሥጋችን ሳለን በሥጋ ፈቃድ እንኖር ዘንድ አይገባም፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞታላችሁ፤ ነገር ግን በመንፈሳዊ  ሥራ የሥጋችሁን ፈቃድ ብትገድሉ ለዘለዓለም በሕይወት ትኖራለችሁ፡፡ በእግዚአብሔር መንፈስ የሚሠሩ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው፡፡ሮሜ 8፣12-14፡፡ እንግዲህ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን እንዲህ ነው! ስለ ጸጋ፣ ስለ እምነትና ስለ በጎ ምግባራት ይነግረናል፡፡ በጸጋ ስለ መዳን፣ በእምነት ስለ መዳንና በበጎ ምግባራት ስለ መዳንም ይነግረናል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ግን አንደኛውን ብቻ ነጥሎ መዳን በጸጋ ብቻ፣ ወይም በእምነት ብቻ፣ ወይም በበጎ ምግባራት ብቻ ነው ብሎ ግን አይነግረንም፡፡ በዚህም የተነሳ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን መዳን በጸጋው፣ በጸጋው ላይ ባለን እምነትና ከእምነታችን የተነሳ በምናደርጋቸው በጎ ምግባራት እንደሆነ ታስተምራለች፡፡
ቁ 16-17 እኛስ የእግዚአብሔር ፍቅር ከእኛ ጋር እንዳለ አውቀን አምነናል፤ እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ በፍቅር የሚኖርም ከእግዚአብሔር ጋር በፍቅር ይኖራል፤ እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ይኖራል፡፡ በዚህም በፍርድ ቀን በእርሱ ዘንድ መወደድን እናገኝ ዘንድ ከእኛ ጋር ያለችው የእግዚአብሔር ፍቅር ትፈጸማለች፡፡  እግዚአብሔር እርሱ ራሱ አስቀድሞ እንደወደደንና ስለመዳናችን አንድ ልጁን ቤዛ አድርጎ እንደሰጠልን እናምናለን፡፡ በዚህ እምነታችንም ደግሞ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘትና ልጆቹም ለመሆን ስንል ወንድሞቻችንን እንወዳለን፡፡ ክርስቶስ የሁሉ ራስ ነውና፤ እኛም ሁላችን ደግሞ ራስ የሚሆን የክርስቶስ የአካሉ ብልቶች ነንና፡፡ በአካሉ ወስጥ ያለውን አንደኛውን ብልት ወንድማችንን ብንጠላ ራስ ወደሚሆነው ክርስቶስ ልንደርስ አንችልምና ወንድሞቻችንን ሁሉ እንወዳለን፡፡ እናምናለን፤ ባመንነው ደግሞ ጸንተን ላመንነው እንታዘዛለን፤ ባመንነው እንኖራለን እንዳመንን እንዲሁ ደግሞ እናደርጋለን፡፡ ከዚህ የወጣ ሁሉ ከክርስትና የወጣ ነው፡፡ ክርስትና ጸጋ ብቻ፣ ወይም እምነት ብቻ፣ ወይም በጎ ምግባራት ብቻ አይደለምና፡፡ ክርስትና ጸጋ፣ እምነትና በጎ ምግባራት በአንድ ላይ ነው እንጂ፡፡
ይትባረክ እግዚአብሔር አምላከ አበዊነ!
 . . . ይቀጥላል . . .


ቅዳሴ ቄርሎስ (ክፍል ሁለት)



ቅዳሴ ቄርሎስ (ክፍል ሁለት)
ይህን ንጹሕ ቅዱስ መስዋዕት በፊትህ እናቀርባለን፤ ስለ አቤልና ስለ ሴት፤ ስለ ሄኖክ፤ ስለ መልከ ጼዴቅም፡፡ ስለአብርሃም፣ ስለ ይስሐቅና ስለ ያዕቆብ፤ ስለ ሙሴና ስለአሮን፤ ስለ ነቢያትም ሁሉ፡፡ 
ስለ ስምዖን ጴጥሮስ፤ ስለ ዮሐንስ መጥምቅም፤ ስለ ሐዋርያትም ሁሉ፡፡
ስለ ዳዊትና ሕዝቅያስ፤ ስለ ኢዮስያስና ስለ ንጉስ ቆስጠንጢኖስ፤ በቀናች ሃይማኖት ስለሞቱት ነገሥታት ሁሉ፡፡
ስለ ኤጲስ ቆጶሳት፤ ስለ ቀሳውስትና ስለ ዲያቆናት፤ ስለ ንፍቀ ዲያቆናትና ስለ አናጉንስጢሳውያን፤ ስለ ወራዙትና ስለ ደናግልም ሁሉ፡፡
መንፈስ ቅዱስ በላይዋ ስላደረባትና የሕይወት መንፈስ ስለ ተፈጸመላት ነፍስ፡፡ በምትወደው በልጅህና በወዳጅህ፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምሳል ስለ ተቀረጸች መልክ ሁሉ፡፡
ይህ ቁርባን ስለ ተደረገላቸው፤ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንህ ስላገቧቸውና ደገኛ ቅዱስ ወደሚሆን ወደ መሠውያህ ፊት ስላቀረቧቸው ቅዱሳንም ሁሉ፡፡
በቀናች ሃይማኖት በምድር ላይ ሁሉ ስለሚኖሩ ስለ መንገደኞችና ስለ ስደተኞችም ሁሉ፤ ከዚህ ዓለም የወጡ፡፡
በምትወደው በልጅህና በወዳጅህ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም ስላመኑ አፍና አንደበት ሁሉ፡፡ ከርሱ ጋራ ክብር ያለው ሥውር ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ፤ ለዘለዓለሙ፡፡
ለእነርሱም ለሁሉም፤ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ቤተ ክርስቲያንህ ትሰግድልሃለች፣ ሙሽራህም ከፍ ከፍ ታደርግሃለች፡፡ በልዑላን ጥቅም፤ በሱራፌል ቅዳሴና በኪሩቤል ውዳሴ፤ በመላእክትም ምስጋና፤ በትጉሃን ልመና፤ በቅዱሳንም ፍጹምነት፡፡
በአዳም ንጽሕና፤ በኖኅም መሥዋዕት፤ በአብርሃም እንግዳ ተቀባይነት፤ በይስሐቅ ቸርነት፤ በያዕቆብ መገለጽ፡፡
በዮሴፍ እስራት፤ በኢዮብ ትዕግሥት፤ በሙሴም የዋህነት፤ በኤልያስም ምስጋና፡፡
በሐዋርያትም ማፍቀር፤ በቅዱሳንም ልመና፤ በተሰደዱ ሰዎች ድካም፤ ባልበደሉ ሰዎች ጽድቅ፤ ንጽሕናን ባገኙ ሰዎች ትሕትና፡፡
በንጹሓን ገድል፤ ከምግብ በተለዩ ሰዎች ትህርምት፤ ፍጹማን ስለሆኑ ቅዱሳን ጽድቅ ፡፡
በምድር ዳርቻ ርቀት፤ በባሕር አዝዋሪ ጥልቅነት፤ በመባርቅት ብልጭታ፤ በደመናትም መውጣት ፡፡
በመላእክት ምስጋና፤ በቅዱሳንም ምስጋና፤ በትጉሃን ንጽሕና በልዑላንም መስማማት፤ በመንፈሳውያን ብርሃን ፡፡
በካህናት ቀኝ፤ በሰማዕታት መሞት፤ በምዕመናንም ደም፤ በብርሃናውያን መላእክትም ገናንነት ፡፡
በልጅህ መመታት (ተጸፍኦ)፤ በአንድ ልጅህ ሕማማት፤ ሁሉን በያዘ ሥልጣንህም ፡፡
ወደ ጌታችንና ወደ መድኃኒታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ አባት በምታርግ ጸሎት ፡፡
እርሱን በሚያሲዙባት በዚያች ሌሊት ፡፡
ክቡራትና ብፁዓት በሚሆኑ እድፍ በሌለባቸው እጆቹ ኅብስቱን ያዘ፤ ወደ አንተ ወደ አባቱ ወደ ሰማይ አቅንቶ አየ፡፡
አመሰገነ ባረከ ቆረሰ ፡፡ አላቸውም ንሡ ብሉ ይህ ኅብስት እማሬ ኃጢአት በሚሠረይ ገንዘብ ለዓለሙ ሁሉ ቤዛ ስለእናንተ የሚፈተት ሥጋዬ ነው፡፡
ዳግመኛም ራታቸውን ከበሉ በኋላ ጽዋውን ይዞ አመሰገነ፤ ባረከ፤ አከበረም፡፡ ደቀመዛሙርቱንም አላቸው ንሡ ጠጡ ይህ ጽዋ፤ እማሬ ኃጢአትን ለማስተሥረይ ስለእናንተ የሚፈስና ለዓለሙ ሁሉ ቤዛ የሚሰጥ ሐዲስ ሥርዓት የሚሆን ደሜ ነው፡፡
የሚነድ የእሳት ሰይፍ ሜሎስ (መንፈስ ቅዱስ) ይገለጽ፤ ሰማየ ሰማያትም በቸርነትህ ይከፈት፤ በፈቃድህም ሕያውና ቅዱስ መንፈስህ ይላክ፤ ይውረድ፤ ይምጣም። በዚህም ኅብስትና ጽዋ ላይ ይረፍ ይባርከው ይቀድሰውም፤ ከአንድ ልጅህ ከጌታችንና ከአምላካችን ከመድኃኒታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋና ደም ጋራ አንድ ይሆን  ዘንድ። ለሚቀርቡት የበደል ማስተሥረያለሚቀበሉትም የኃጢአት ይቅርታ ይሆን ዘንድ ።
በቀናች ሃይማኖት አን ሆነው ከርሱ ለሚቀበሉ ሰዎች ሁሉ ለይቅርታና ለምሕረት ለደኅንነትና ለረድኤት፤ ለነፍስና ለሥጋ ሕይወት ይሁንላቸው፡፡ ለበደል ማስተሥረያ፤ ለኃጢአት ይቅርታ፤ ለትንሣኤ ሙታንና ለሐዲስም ሕይወት ይሁንላቸው፤ ለዘለዓለሙ።
ግመኛም ሁሉን የሚይዝ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አባት እግዚአብሔርን እንማልዳለን። አቤቱ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ እየተመኘን ዐይኖቻችንን ወደአንተ እንሰቅላለን። በአብራከ ልቡናችንም እንሰግድልሃለን የኅሊናችንንና የመንፈሳችንን ራስ እናዋርድልሃለን ።
አቤቱ በቅድስናህ ቀድሰን በምሕረትህም አንጻን፤ ቅዱስ ምስጢርህንም ለመቀበል የተገባንና አንድ የሆን አድርገን ።  
በቅዱስ መሠውያህ በፊትህ ያኖርነው ይህ የእሳት ፍሕም የሚከሰን አይሁን። የፈተትነው ይህ የአምልኮ ኅብስት ለበቀል አይሁንብን ነፍችንንና ሥጋችንን ስላላነን ።
የሚያቃጥል እሳትን ለመብላት የጋለ ፍሕምንም ለመዋጥ ከንፈርን መክፈት የሚያስፈራ ነው። ነፍስ ውስጥዋን ከሽንገላ ካላነጻች ።
በድንኳኑ ውስጥ የንጹሕ ሙሽራን መሠዋቱን ማየት የሚያስፈራ ነው ።
ሕያው የሚሆን የአምላክን ልጅ በሰማያዊ አባቱ ፊት መሠዋቱን ማየት  የሚያስፈራ ነው ።
የመለኮትን ብልጭታ መቅረብ፤ የጌትነት ብርሃንንም (መብረቅመንካት የሚያስፈራ ነው ።
ለመያዙ ራሳችንን እናንጻ ለመቀበሉ ነፍሳችንን እንቀድስ ንጹሕ መግዝዐ ላህም ሆኖ ይሠዋ ዘንድ ለወደደ አብ ምስጋና ይገባዋል እንበል ።
ለወልድም ምስጋና ይገባዋል፤ ይውም ንጹሕ የሚሆን መግዝዐ ላህም ነው፡፡ ይህን ኅብስት ንጹሕ የሚሆን የመግዝዐ ላህም ሥጋ ላደረገው ለመንፈስ ቅዱስም ምስጋና ይገባዋል ።
ሦስት ስም አንድ እግዚአብሔር ነው፤ ሦስት ገጽ አንድ መልክ፤ ሦስት አካል አንድ ባሕርይ ነው ።
በትጉሃን መላእክት አፍ መመስገን ይገባዋል፤ በነቢያትና በሐዋርያትም አፍ መመስገን ቅዱስ መባል ይገባዋል ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘለዓለሙ እስከ ሁለተኛ ጉባኤ ድረስ ።
አብ ከልጁ ጋራ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ከሰዓትና ከዕለት ከአውራኅና ከዓመታት አስቀድሞ የነበረ ነው ።
በአነዋወር ለአንዱ ከሁለተኛው፤ ለሁለተኛውም ከሦስተኛው መቅደም የለም። የመባርቅት ፍጥነታቸው ምን ያህል ነው። የንሥር ክንፎች ፍጥነት ምን ያህል ነው።
ባለመለያት አንድ ናቸው፤ ባለመቀላቀልም አንድ ናቸው፤ በሦስትነት ይኖራሉ፤ ባንድነት የተያያዙ ናቸው፤ በአካል የተካከሉ ናቸው፤ በብርሃንና በፀዳል የተመሳሰሉ ናቸው ፡፡
አብ ልጁን ዓለም ሳይፈጠር የወለደው በሥራ ሊረዳው አይደለም፡፡ የመንፈስ ቅዱስም ባሕርይ የተገኘ ብልሃትና ሥራ ለማወጣጣት አይደለም፡፡
ከእግዚአብሔር አብ ብቻ መወለዱን እንናገር፤ ያን ጊዜ እናት አልነበረችውም፤ የፍጡራን አነዋወር ገና አልታየም ነበርና፤ ዳግመኛም ምድራዊ አባት ሳይኖረው የአምላክ ልጅ ብቻውን ከዳዊት ልጅ ከድንግል ብቻ መወለዱን እንናገር፤ እናውራ ፡፡
በዘር ለመወለድ አባት ስላልነበረው የሰውነት ሥራ አልጎደለበትም፤ ከድንግል ብቻ ፈጽሞ ሰው ሆነ እንጂ፡፡
ከአዳም ጎን አጥንት በተፈጠረች ጊዜ እናት ስላልነበረቻት ሔዋን የሴቶች ባሕርይ እንዳልጎደለባት፤ እንዲሁ የአዳምን አባት በሥጋ በወለደችው ጊዜ የማርያም ማኅተመ  ድንግልናዋ አልጎደለም ፡፡
አዳምን የጎኑ አጥንት በተነቀለ ጊዜ እንዳላሳመመው እንደዚሁ የገሊላ ወገን የምትሆን የአምላክን እናት ሕማመ ወሊድ አላገኛትም ።
እንዲህ እናምናለን እንዲህም እንታመናለን ይህ የምንፈትተው ኅብስት ከዕብራውያን ልጅ የነሣው የክርስቶስ ሥጋ እንደ ሆነ ።
ዳግመኛም ይህ ጽዋ የእግዚአብሔር በግ ከሚሆን የፈሰሰ ደመ መለኮት እንደሆነ እናምናለን፤ ዳግመኛም ይህ ትእምርተ መስቀል በሕማማቱ ጊዜ የተዘረጋ የክርስቶስ የመስቀሉ ምሳሌ እንደ ሆነ እናምናለን ።
ደምን የተረጨች ልብስን ለለበሰ ለርሱ በመሠዊያው ፊት እንሰግዳለን ደምን ለተረጨች ለዚያችም ልብስ ለዘለዓለሙ ።
ያን ጊዜ ከዚህ ከማይጠፋ ምሥጢር የተቀበልን የእኛ አፋችን ደስታን ተመላ አንደበታችንም ደስ አለው ።
አቤቱ ዓይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልቦናም ያልታሰበውን ቅዱስ ስምህን ለሚወዱ ሰዎች ያዘጋጅህ አምላክ ምን ትደነቅ። በቅድስት ቤተ ክርስቲያንህ ላለን ለታናናሾች ሕፃናት ለእኛ ገለጽህ፤ አብ ሆይ ይህ ፈቃድህ በፊትህ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር አንተ ይቅር ባይ ስለ ሆንህ ነውና።
ለአንተም እስከ አርያም ድረስ ምስጋናን ክብርንም ለአብና ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስም እናቀርባለን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ ።
የጠራኸንንና የቀደስኸንን እኛን አቤቱ በአጠራርህ ዐድለን፤ በፍቅርህ ጠብቀን በምስጋናህም አጽናን ።
ከክፉ ነገር ሁሉ ጠብቀን በዘለዓለም መንግሥትህ በልጅህ በክርስቶስ በቀኝህ አድነን፡፡ ርሱ ያለ ክብር ጽንዕ ለአንተ ይገባል ርሱ ጋራ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ዛሬም ዘወትርም፤ ለዘለዓለሙ ።

ትምህርተ ንስሓ (ክፍል አንድ)




ትምህርተ ንስሓ (ክፍል አንድ)

ንስሓ፦ ነስሓ/ተጸጸተ ከሚለው የግዕዝ ግስ/ቃል የተገኘ ሲሆን፤ በሠሩት ኃጢአት መጸጸት፣ ማዘን፣ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ መወሰን ማለት ነው። በአንቀጸ ንስሓ እንደተገለጸው ንስሓ መናዘዝ፣ ኑዛዜ ማደረግ፣ ወይም ኃጢአትን ለአበ ነፍስ (ለካህን) መናገርና ራስን መግለጥ ነው፡፡ በትንቢተ ሕዝቅኤል ላይ ኃጢአተኛውም ከሠራው ኃጢአት ቢመለስ ፍርድንና ቅን ነገርንም ቢያደርግ ነፍሱን ይጠብቃል፡፡ አስቦ ከሠራው በደል ሁሉ ተመልሷልና ፈጽሞ በሕይወት ይኖራል እንጂ አይሞትም በማለት የሰፈረው ቃል የንስሓ ሕይወትን ምንነት በጉልህ ያስገነዝባል (ሕዝ.18.27-29)፡፡ በዚሁ መጽሐፍ በምዕራፍ 33 ቁጥር 16 ላይ የሠራው ኃጢአት ሁሉ አይታሰብበትም ይላል፤ ስለሆነም በኀጢአታችን ስንናዘዝና ንስሓ ስንገባ እግዚአብሔር ይተውልናል፣ ይቅርም ይለናል፤ ባልተናዘዝንበትና ንስሓ በልገባንበት ኀጢአት ግን እግዚአብሔር አምላካችን ያዝንብናል፣ ስላለመናዘዛችንም ይቀጣናል፡፡ ንስሓ ለተጠመቁ ሰዎች ከጥምቀት በኋላ የተሰጠች ሀብት ናት። በጥምቀት ከእግዚአብሔር ከምትገኝ ልጅነት ቀጥላ ያለች ሁለተኛ ማዕረግ ናት፡፡ በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጆች ሆነን እንደምንወለድ ሁሉ በኃጢአትና በበደል የምናጣትን ልጅነታችንን በንስሓ መልሰን እናገኛታለንና ከጥምቀት በኋላ የእግዚአብሔርን ልጅነት የምታስገኝ ሁለተኛ መዐርግ ትባላለች፡፡ ንስሓ በሃይማኖት ገንዘብ የምናደርጋት የመንግሥተ ሰማያት መግዣ ናት፤ በንስሓ የእግዚአብሔርን መንግሥት እንወርሳታለንና። ንስሐ ለሚሿት ሰዎች የተከፈተች የይቅርታ በር ስትሆን ከፈጣሪ ወደሚገኝ ቸርነትና በጎነት እንገባባታለን/እንቀርብባታለን፡፡

ምሥጢረ ንስሓ ማለት አንድ ሰው ከጥምቀት በኋላ የፈጸመውን ጥፋት አውቆ ሁለተኛ ጥፋቱን ላለመድገም ወስኖ በእግዚአብሔርና በካህኑ ፊት ተንበርክኮ ከልቡ ተጸጽቶ ኃጢአቱን በመናዘዝ ከኃጢአቱ እስራት የሚፈታበትና ከእግዚአብሔር ይቅርታን የሚያገኝበት ታላቅ የይቅርታ ምሥጢር ነው። ምሥጢር መባሉም በአይናችን በምናየውና በምናስተውለው የንስሓ ሥርዐት መንፈሳዊና ረቂቅ የሚሆን ሥርየተ ኀጢአትን/የኀጢአት ይቅርታን ስለምንቀበልበት ነው፡፡ ንስሐ ከእግዚአብሔር የሚሰጥ እግዚአብሔርን የሚያስወድድ፤ ከንጹህ ልብ የሚመነጭ ጸጋ ነው። እግዚአብሔር አምላካችን ሐዳጌ በቀል/ኀጢአትን ቅር የሚል መሆኑን የምንረዳበት መንገድ ስለሆነ በፊት ከነበረው ሕይወታችን በተሻለና በበለጠ ሁኔታ በንስሓ ወደ እግዚአብሔር እንቀርባለን፤ ፍቅሩንም እያሰብን የበለጠ እንወደዋለን፡፡ ሕዝ 36፡25-27፡፡ ንስሓ ከኃጢአት እንቅልፍ መንቃት ሲሆን (ሮሜ 13፡11) ሰዎች ስለ ኃጢአታቸው ተጸጽተው ከእግዚአብሔር ጋር እንዳይታረቁና ወደሚወዳቸውና ወደሚቀበላቸው አምላክ እንዳይመለሱ በብርቱ በሚጥረው ሰይጣን ላይ የተገኘ ድልም ነው። መዝሙር 123፣ 6-7፡፡ ንስሓ ከኃጢአትና ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ በመውጣት (ዮሐ 8፣34-36) ወደ መንፈሳዊ ሕይወት ተመልሶ (ኤፌሶን 5፣14) ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅና (2ኛቆሮ 6፣19) ወደ እግዚአብሔር መቅረብና መመለስ ነው። (ሚል 3፣7)፡፡

የምሥጢረ ንስሓ አመሠራረት
ምሥጢረ ንስሓን የመሠረተ ራሱ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ለሰው ልጆች ሁሉ የሚራራና የሚያዝን መፍቀሬ ሰብእ ክርስቶስ የእኛን ኃጢአት ሁሉ በሰውነቱ ተሸክሞ በሕማምና በሞቱ አንድ ጊዜ አድኖናል፤ በዚህም የተነሳ ልጅነታችን ተመልሶልናልና ዳግመኛ የእግዚአብሔር ልጆች የምንሆንበት ዕድል ተሰጥቶናል፤ ይህንንም ጸጋ በምሥጢረ ጥምቀት አግኝተነዋል። ከዚህ በኋላ ለምንፈጽመው በደል ማስተሥረያ እንዲሆነን ለሐዋርያትና በእነርሱ እግር ለተተኩት ካህናት ሥልጣንን በመስጠት ምሥጢረ ንስሐን መሥርቶልናል። ኃጢአትን የማስተስረይ ሥልጣን የእግዚአብሔር ብቻ ሲሆን ለእኛ ጥቅምና ደህንነት ሲል ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ለጴጥሮስና ለሐዋርያት ተከታዮች የክህነትን አገልግሎት ሰጥቷል። ቅዱስ ጴጥሮስ ስለእውነተኛ እምነቱ ከመሰከረ በኋላ ሥልጣነ ክህነትን ማለትም የመንግሥተ ሰማያትን ቁልፍ ክርስቶስ ሰጥቶታል። እንዲህም ብሎታል የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻዎች እሰጥሃለሁ በምድር የምታስረው ሁሉ በሰማያት የታሰረ ይሆናል፤ በምድርም የምትፈታው ሁሉ በሰማያት የተፈታ ይሆናል ማቴ 16፣19፡፡  እንደዚሁም ይህን ሥልጣን ለሌሎች ሐዋርያትም ሰጥቷቸዋል። ማቴ 18፣18፡፡ ከትንሣኤው በኋላም ለሦስተኛ ጊዜ ኃጢአትን የማስተስረይ ሥልጣን ሰጥቷቸዋል። አብ እኔን እንደላከኝ እኔም ደግሞ እልካችኋለሁ አላቸው። ይህንንም ብሎ እፍ አለባቸውና መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ። ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው። 20፣21-23፡፡ ስለዚህ ኃጢአትን የማስተሥረይ ሥልጣን ለእነሱ የተሰጠ ስለሆነ በሐዋርያት እግር ለተተኩ ለቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ካህናት ኃጢአትን መናዘዝ ይገባል።

የንስሐ ዓላማ በራሳችን ድካም የሠራነውን በደል ዕገሌ አሳስቶኝ እያሉ ሌላውን ሰው ስለ እኛ ስህተት ተጠያቂ ማድረግ ሳይሆን፣ አንደበታችንን ከሳሽ፣ ህሊናችንን ምስክር፣ አድርገን በመጨከን ራሳችንን በእግዚአብሔር ፊት መክሰስ ነው። ከሰዎች ተሸሽገን የበደልነውን በደልና የፈጸምነውን ኀጢአት ካህኑን ምስክር አድርገን በእግዚአብሔር ዳኝነት ፊት መቅረብ ነው፡፡ ከሰዎች ተሸሽገን የበደልነውን በደል በካህኑ ፊት በምንናገር ጊዜ ነፍሳችን ስለምታፍርና ስለምትሸማቀቅ ምህረቱ ብዙ የሚሆን አምላካችን እግዚአብሔር ይህንን የልባችንን መመለስ አይቶ የሠራነውን በደል ሁሉ እንዳልተሠራ አድርጎ ያነጻናል ። በደልንና መተላለፍን በንስሓ ይቅር ማለት የእግዚአብሔር የቸርነት ሥራ ነውና በካህኑ ፊት ማፈሯንና መሸማቀቋን ለነፍሳችን እንደቅጣት ይቆጥርላትና ሥርየትን/የኃጢአት ይቅርታን ይሰጣታል፡፡  

ኃጢአትን ለመምህረ ንስሓ መናገርን ወይም መናዘዝን እንደ ስሕተት የሚቆጥሩና ሌላ ወኪል ምን ያስፈልጋል፣ እኔ ራሴ በቀጥታ ለእግዚአብሔር አልነግረውምን? . . . ብለው የሚከራከሩ ሰዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ሐሳባቸው ከቅዱሳት መጻሕፍት ቃል ውጭ ስለሆነ ፈጽሞ ተቀባይነት የለውም። ኀጢአቱን የሚሰውር አይለማም፤ የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል። ምሳ 28፣13 ተብሎ እንደተጻፈ ኀጢአትን መናዘዝ ተገቢ ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡  በሌላም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እርስ በርሳችሁ በኀጢአታችሁ ተናዘዙ ተብለን ስለታዘዝን ኀጢአታችንን ለመምህረ ንስሓችን እየተናዘዝን ሥርዐተ ንስሓን እንፈጽማለን፡፡ ያዕ 5፣16፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ የንስሓ ጥምቀትን በሚያጠምቅበት ጊዜም ሕዝቡ ሁሉ ከመጠመቃቸው በፊት ኀጢአታቸውን ይናዘዙ አንደነበረም ከመጽሐፍ ቅዱስ እናነባለን፡፡ ማቴ 3፣6፤ ማር 1፤5፡፡

ንስሓ እንዴት ይፈጸማል?

እንግዲህ ንስሓ ገብተን፣ የኃጢአትን ሥርየት አግኝተን፣ ከሰውና ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀን በጽድቅ ጎዳና ለመራመድና በደኅንነት ጸጋ ለመኖር እንድንችል ቢያንስ ሦስት ነገሮችን መፈጸም አለብን። የመጀመሪያው የንስሓ ኀዘን ወይም እውነተኛና ልባዊ ጸጸት ሲሆን ይኸውም ስለክፉ ሥራችንና ስለመተላለፋችን የምንጸጸትበትና በደላችንን የምናምንበት ነው፡፡ መበደላችንንና መተላለፋችንን ሳናምንና ጥፋተኛነታችንን ሳንቀበል ወደሚቀጥለው የንስሓ ሥርዐት ልንደርስ አንችልምና፡፡ ሁለተኛው ኑዛዜ ሲሆን የበደልነውን በደልና ክፉ ሥራችንን ሁሉ ካህኑን ምስክር አድርገን በእግዚአብሔር ዳኝነት ፊት የምንናዘዝበትና ራሳችንን ጥፋተኛ አድርገን የምናቀርብበት መንገድ ነው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ ስለኃጢአታችን የሚሰጠንን የንስሓ ቅጣት የሚመለክት ሲሆን የሚሰጠንን ቀኖና/ሥርዓት መፈጸምና ከዚህ በኋላ በካህኑ በኩል የምናገኘው የፍትሐት/ከኃጢአት እስራት የመፈታት/ ጸጋ ነው። እግዚአብሔር ኀጢአታችንን ይቅር እንደሚለንና ምህረትን እንደምንቀበል ማመናችን የተሰጠንን ቀኖና በመንፈሳዊ ታማኝነትና በእምነት በመፈጸማችን ይታወቃል፡፡

ንስሐ የሚገባ ሰው በመጀመሪያ ኀጢአቱን እያስታወሰ፣ ሰውና ፈጣሪውን መበደሉን እያሰበ የሚያደርገው ኀዘን ወደ ንስሐ የሚወስድ እውነተኛ ኀዘን ስለሆነ ኀዘኑን እግዚአብሔር ይቆጥርለታል። የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው፣ መጽናናትን ያገኛሉና ማቴ 5፣4 የተባለው የራሳቸውንና የሌላውን ኃጢአት እያሰቡ የሚያዝኑትን ተነሳሒያን ይመለክታል። ስለእውነተኛው ኀዘን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደሚከተለው ያስተምረናል፡- አሁን ግን ስለ እርሷ በብዙ ደስ ይለኛል፡፡ ደስታዬም ስለአዘናችሁ አይደለም ንስሓ ልትገቡ ስላዘናችሁ እንጂ፤ ከእናንተ አንዱ ስንኳ እንዳይጠፋ ስለእግዚአብሔር ብላችሁ አዝናችኋልና፡፡ ስለእግዚአብሔር ተብሎ የሚደረግ ኀዘን የዘለዓለም ሕይወትን የሚያሰጥ ንስሓ ነው፡፡ 2ኛ ቆሮ 7፣9-10፡፡ እንግዲህ ከዚህም በኋላ ተነሳሒው እውነተኛውን ኀዘን ከእንባ ጋር አድርጎ በንጹህ ልቦናና ጸሎት ለእግዚአብሔር በማቅረብ እንደገና ላለመበደል መወሰን ይኖርበታል። ውሳኔውንም ለመፈጸም የሚያስችለውን የመንፈስ ቅዱስን ረድኤት ለማግኘት ሁልጊዜ ተግቶ መጸለይ አለበት።

ከዚህ ቀጥሎ ተነሳሒው ኃጢአቱን ሥልጣነ ክህነት ላለው ካህን ይናዘዛል። ኑዛዜ ማድረግ በቅዱሳት መጻሕፍት የታዘዘ ነው። ከእነዚህ ነገሮች በአንዲቱ በደለኛ ቢሆን፥ የሠራውን ኀጢአት ይናዘዛል። ስለሠራው ኀጢአት ለእግዚአብሔር የበደልን መስዋዕት ያመጣል፤ … ካህኑ ስለኀጢአቱ ያስተሠርይለታል። … እርሱም ይቅር ይባላል።ዘሌ 5፣5-10፡፡ የኀጢአትን ሥርየት ለማግኘት ለካህን መናዘዝ እንደሚገባ መጽሐፍ ቅዱስ ስለሚያስተምረን ኃጢአታችንን ለአናዛዡ ካህን ከበደሉ ዓይነትና ሁኔታ ጋር ማስረዳት ይገባናል። ስንናዘዝም ከእንባና ከጸጸት ጋር ሆነን ከካህኑ ጋር አብሮ እግዚአብሔር እንደሚሰማን አምነን በእውነት መናገር ያስፈልገናል። በሽታውን የሰወረ መድኃኒት አያገኝም እንዲሉ ለነፍስ ቁስል ሐኪም ለሆነው ለካህኑ ኀጢአታችንን ከሰወርን ለነፍስ የሚሆነውን ፈውስ ለማግኘት አንችልም። ኀጢአቱን የሚሰውር አይለማም፤ የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል። ምሳ 28፣13 ተብሎ ተጽፏልና ከቂምና ከበቀል በመራቅ፣ የበደልነውን እየካስን፣ የበደለንን ደግሞ ይቅር እያልን ብንናዘዝና የሰማዩን አባታችንን በጸሎት ብንጠይቀው ምሕረትና ፈውስን፤ ለኀጢአታችንም ሥርየትንና ይቅርታን ይሰጠናል። ነገር ግን እኛ ማንንም አልበደልንም ኃጢአትም የለብንም ብንል እግዚአብሔርን ሐሰተኛ ማድረጋችን ስለሆነ እንጠንቀቅ። ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ እንዳለው ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፣ እውነትም በኛ ውስጥ የለም። በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው። ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በኛ ውስጥ የለም። 1ኛ ዮሐ 1፣8-10፡፡

ምንጭ፡-
1) መጽሐፍ ቅዱስ
2) የንስሓ ሕይወት - በዲ/ን እሸቱ ታደሰ
3) የንስሓ በር - በመ/ር ተስፋሁን ነጋስህ
4) ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት - በሊቀ ጉባዔ አባ አበራ በቀለ


ይትባረክ እግዚአብሔር አምላከ አበዊነ!

 . . . ይቀጥላል . . .