ጸሎት ለመንፈሳዊ ሕይወት ዕድገት
ጸሎት ምንድን ነው? ጸሎት ጸለየ ከሚለው የግዕዝ ቃል የተገኘ ሲሆን
ትርጉሙም መለመን፣ መማጸን የሚለውን ትርጉም ይሰጠናል፡፡ ጸሎት
ሰው ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብበትና የሚነጋገርበት መንፈሳዊ መንገድ
ነው፡፡ ጸሎትስ ሰው ከልዑል እግዚአብሔር ጋር የሚነጋገራት ነገር ናት፡፡ ፈጽሞ እያመሰገነ ጌትነቱን አውቆ በደሉን አምኖ እርሱን
ደስ የሚያሰኝበትንም ሽቶ የሚነጋገራት ነገር ናት (ፍትሕ መንፈሳዊ አን 14 ቁ 528)፡፡ ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት እንድንቆምና
ከአምላካችን ጋር እንድንነጋገር የሚያስችለን ታላቅ መንፈሳዊነት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ‘‘አቤቱ፥ ፊትህን እሻለሁ ልቤ
አንተን አለ።’’ እንዳለ ጸሎት ዘወትር የእግዚአብሔርን ፊት መሻት ነው፡፡ መዝ 27፣8፡፡
ስንጸልይ ከአምላካችን ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር እንችላለን፤ ይህም ንግግራችን ለሕይወታችን ምሪትን የምንቀበልበት ነው፡፡ ጸሎት
ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ መንገድ ነው፡፡ ዘወትር የሚጸልይ ሰው ወደ እግዚአብሔር ሳይደርስ አይቀርም፡፡ ‘‘በጥዋት ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትደርሳለች።’’
እንዳለ ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔርን የምትሻ ነፍስ ዕለቱን በእግዚአብሔር ፊት በመሆንና ከእርሱም ጋር በመነጋገር ትጀምረዋለች፡፡
መዝ 88፣13፡፡ ጸሎት የሰው ልጆች ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት ድልድይም ነው፡፡ ከስጋዊ ሃሳብና ድካም ርቀን
ወደ እግዚአብሔር ለመድረስ በመንፈስ የምንሻገርበት መንፈሳዊ የመሸጋገሪያ ድልድይ ነው፡፡ ልክ ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ እንዳያው መሰላል ከምድር አስከ ሰማይ የሚደርስ
መወጣጫም ነው፡፡ በምድር ላይ ሳለን በመንፈስ ከፍ በማለት ወደ ሰማይ የምንደርስበትና በአምላካችን ፊት የምንሆንበት፣ ከእግዚአብሔር
የሆነውን ሰማያዊ ሃሳብ የምንቀበልበት የመወጣጫ መሰላል ነው፡፡ ጸሎት የቃላት ንግግር ብቻ ሳይሆን በጠለቀ መረዳትና በታላቅ ተመስጦ
ውስጥ ሆነን ነፍሳቸንን፣ ሐሳባችንንና ስሜታችንን ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት የምናደርግበት መንፈሳዊ ተግባር ነው፡፡
ምንም እንኳን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ መንገድ ቢሆንም ሁሉም
ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያደርሳል/ያቀርባል ማለት አይደለም ፡፡ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ሊያደርስና ኃይል ሊኖረው የሚችለው እንደፈቃዱ ሆነን ስንለምንና በፈሪሀ እግዚአብሔር
መጸለይ ስንችል ብቻ ነው፡፡ ‘‘የጻድቅ
ሰው ጸሎት በስራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች፡፡’’ ያዕ 5፣16 ተብሎ እንደተጻፈ ኃይል የሚፈጸምበት ጸሎት የጻድቅ ሰው ጸሎት ነው፣ የክፉዎችን ጸሎት ግን አምላካችን
ይጸየፋል፡፡ ‘‘እግዚአብሔር
ከኅጥኣን ይርቃል የጻድቃንን ጸሎት ግን ይሰማል፡፡’’ እንዲል ምሳ 15፣29፡፡
ለጸሎት በቆምንበት ቅጽበት ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መቆማችንን እናስባለን፡፡
‘‘በፊቱ የቆምሁት የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር’’ 1ኛ ነገ 17፣1 እንዳለ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት የምንቆምበት እርግጠኛ ሐሳብ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት
መቆማችንን ሳናስብና ሳናምን ለጸሎት በፊቱ አንቆምምና፡፡ ጸሎት ከውስጣችን የሚመነጭ የነፍሳችንና የልባችን መቃተት እንጂ የቃላት ንባብና ድግግሞሽ አይደለም፡፡
ጸሎት በመንፈስ የምንረዳው እንጂ በቃላት ውበት የምንገልጸውና የምናስረዳው ተራ ድርጊት አይደለም፡፡ ማስመሰል በሌለበት እውነተኛ
ስሜት ውስጥ ሆነን፣ በተመስጦ፣ በማስተዋልና በመረዳት፣ በተሰቀለ ኅሊና፣ በተሰበረ መንፈስ፣ ስለኃጢአቱ በተጸጸተ ልብ ወደ አምላካችን
የምንጠጋበት መጠጋትና ከፈጣሪያችን ጋር የምንነጋገርበት መነጋገር ስለሆነ
ጸሎት በተግባር የሚገለፅ ታላቅ መንፈሳዊነት እንጂ ተራ የቃላት ስብስብ አይደለም፡፡ ጸሎት በመንፈስና በነፍስ ከእግዚአብሔር
ጋር መነጋገር ነውና በዝምታ ውስጥ ሆነን እንኳን በህሊናችንና በሃሳባችን ወደ እግዚአብሔር ደርሰን ልንነጋገር እንችላለን፡፡ ጸሎት
እግዚአብሔርን መናፈቅም ነውና ወደ እግዚአብሔር ለመድረስ የምንቸኩልበትና የምንናፍቅበት የነፍስ መሻት ነው፡፡ ‘‘ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፥ አቤቱ፥ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች።’’ መዝ 42፣1፡፡ ጸሎት ወደ ሕይወት ውኃ ምንጭ እግዚአብሔር ለመድረስ
የምንጠማው መጠማት ነውና ከነፍሳችንና ከመንፈሳችን የሚወጣ ጥልቅ ስሜት እንጂ ቃላትና ንግግር ብቻ አይደለም፡፡
‘‘አምላኬ፥ አምላኬ፥ ወዳንተ እገሠግሣለኹ፤ ነፍሴ አንተን ተጠማች፥ ሥጋዬ
አንተን እንዴት ናፈቀች’’ እንዳለ ቅዱስ ዳዊት
ጸሎት ስራ ወይም ልንፈፅመው የሚገባ አስገዳጅ ሕግ ሳይሆን ወደንና ፈቅደን የመንፈፅመው የነፍሳችንና የስጋችን የእግዚአብሔር ናፍቆትና
በፊቱ ለመሆን የምናደርገው መጓጓት ነው፡፡ የሚጸልይ ሰው አምላኩንና በአጠገቡ ያለውን ወንድሙን የሚወድ ነው፡፡ ያለፍቅር የሚጸልይ
ሰው ወደ እግዚአብሔር መድረስ ስለማይችል ጸሎቱ መጽናናትንና የልብ እረፍትን አያመጣለትም፡፡ እግዚአብሔር የአፋችንን ንግግርና የቃላቱን
ማማር ሳይሆን በልባችን ውስጥ ያለውን በጎ ሃሳብ ነው የሚሻው፡፡ ለዚህም ነው ‘‘ይህ ህዝብ በአፉ ወደ እኔ ይቀርባል፣ ልቡ ግን ከእኔ የራቀ ነው’’ ሲል የተናገረው፡፡ ኢሳ
29፣13፡፡ ስለዚህ ጸሎታችንን በፍቅር የሚደረግ፣ የወንድምን በደል ይቅር የሚልና የሚታገስ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡
እግዚአብሔር የእጁ ስራ የሆኑ ፍጥረቱን ሁሉ የሚወድና የሚቀበል ስለሆነ ወንድምን በሚጠላ ልብ የምንጸልየው ጸሎት እግዚአብሔርን
ደስ አያሰኝም፡፡ ብዙ በደላችንን የተወልን ጌታ እኛም የወንድሞቻችንን በደል እንድንተውላቸው ይፈልጋል፡፡ ስለሆነም በተሰበረ መንፈስና
በትሑት ሰብዕና፣ ስለድካሙ በሚያዝንና በሚጸጸት ማንነት፣ ወንድሙን በሚወድና ይቅር በሚል ልቡና ውስጥ ሆነን መጸለይ ካልቻልን ጸሎታችን
በፊቱ ሊወደድልን አይችልም፡፡ ስለዚህም ነገር እግዚአብሔር አምላካችን እንደህ ሲል ተናግሮናል፡- ‘‘እጃችሁን ወደ እኔ ብትዘረጉ ዐይኔን ከእናንተ እሰውራለሁ ልመናንም
ብታበዙ አልሰማችሁም፡፡ እጆቻችሁ በደም ተሞልተዋል ፡፡’’ ኢሳ 1፣15፡፡ ጸሎት ሁሉን በሚችል ጌታ ፊት ከድካማችን
እንዲያበረታንና ከኃጢአታችን ሁሉ እንዲያነጻን ነፍሳችንን በፊቱ የምናፈስበት ማፍሰስ ነው፡፡ ‘‘ልመናዬን በፊቱ አፈሳለኹ’’ እንዳለ ቅዱስ ዳዊት የነፍሳችንንና
የስጋችንን ሁሉ መሻት፣ ጭንቀትና መረበሽ ሁሉ በፊቱ የምናፈስበትና የምናርፍበት ታላቅ እረፍት ነው፡፡ ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት
ድካማችንን የምናምንበትና ምሕረቱን የምንለምንበት የይቅርታና የንስሓ ልመናም ነው፡፡ ይህም እውነቱን በፊቱ በመግለጥ እርቅንና ይቅርታን
የምንቀበልት የትሑታን መንገድ ነው፡፡ እራሱን በማጽደቁ አንዳች ሳይቀበል ወደቤቱ እንደተመለሰው ፈሪሳዊ ሳይሆን ጥፋቱንና ድካሙን
በማመን አምላኩን እንደለመነውና ጻድቅ ሆኖ ወደ ቤቱ ተመለሰ ብሎ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመሰገነው እንደቀራጩ
ሰው ለጸሎት በቆምንበት ቅጽበት ሁሉ በፊቱ መበደላችንንና ሕጉን መተላለፋችንን መርሳት አይገባንም፡፡ሉቃ 18፡13፡፡ ከዚህ ይልቅ ግን እንዲህ ልንል ያስፈልገናል፡-
‘‘አቤቱ፥ እንደ ቸርነትኽ መጠን ማረኝ፤ እንደ ምሕረትኽም ብዛት መተላለፌን ደምስስ። ከበደሌ ፈጽሞ እጠበኝ፥ ከኀጢአቴም አንጻኝ፤
እኔ መተላለፌን ዐውቃለኹና፥ ኀጢአቴም ዅልጊዜ በፊቴ ነውና። አንተን ብቻ በደልኹ፥ በፊትኽም ክፋትን አደረግኹ፥ በነገርኽም ትጸድቅ
ዘንድ በፍርድኽም ንጹሕ ትኾን ዘንድ። እነሆ፥ በዐመፃ ተፀነስኹ፥ እናቴም በኀጢአት ወለደችኝ። እንሆ፥ እውነትን ወደድኽ፤ የማይታይ
ስውር ጥበብን አስታወቅኸኝ። በሂሶጵ ርጨኝ፥ እነጻማለኹ፤ እጠበኝ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እኾናለኹ፡፡’’ መዝ 50፣1-7፡፡
በእንዲህ ያለ መረዳትና ተመስጦ
የምንጸልየው ጸሎት እጅግ ታላቅ የሆነ ኃይልን ያደርጋል፡፡ ያዕ 5፣16፡፡ በመንፈሳዊ ሃሳብና መረዳት የሚደረግ ጸሎት ሁሉ ወደ
እግዚአብሔር ስለሚያደርስ የጠላትን ኃይልና ተግዳሮት ሁሉ ለማሸነፍ ያስችላል፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ የሚደረግን ጸሎት አጋንንት ክፉኛ
ይፈሩታል፡፡
ይቀጥላል …