Tuesday, December 15, 2015

ታላቅ ወንድሜ


እለቱ አርብ ነው፡፡ አምሽቼ ነበር ወደ ቤት የገባሁት፡፡ቤት ወስጥ ማንም ስላልነበረ መኝታ ቤቴ ገብቼ ጋደም ብያለሁ፡፡
‘‘ እሺ  አቤል ክላስ አለቀ ?’’ ታላቅ ወንድሜ ነበር፤ የመኝታ ቤቴን በር ቀስ ብሎ ከፍቶ እየገባ፡፡       
‘‘እንዴት አመሸህ አልዓዛር?’’
‘‘አለሁ ይመስገን፡፡ እማዬ የለችም እንዴ?’’
‘‘ ለቅሶ ቤት ልታማሽ ሄዳለች አለች ስምረት ’’
‘‘ቆይተሀል እንዴ ከመጣህ?’’
‘‘%ረ ገና መግባቴ ነው ’’
‘‘ታዲያ ምነው አመሸህ?’’
‘‘ግቢ ጉባኤ ስብሰባ ነበረኝ’’
‘‘ምን ነበር አጀንዳው ?’’ አልጋዬ ጫፍ ለይ ተቀመጠ፡፡ሁልጊዜም ስለ ግቢ ጉባኤ ከተነሳ የሆነ የሚለኝ ነገር እንደሚኖር እርግጠኛ ነኝ፡፡ እራሱን ምሳሌ እያደረገ የሚነግረኝ ነገሮች ስለራሴ ብዙ እንዳስብ ያደርጉኛል፡፡
       ‘‘ስለ አባላት ጉዳይ ነበር የተወያየነው’’
       ‘‘ስለ አባላት ምን?’’
       ‘‘በአገልግሎት ስለመበርታትና ኃላፊነትን ስለመወጣት  ’’
       ‘‘እና ምን ድምዳሜ ላይ ደረሳችሁ?’’
‘‘ብዙ ነገሮችን አንስተን ተወያይተናል፡፡ በመጨረሻ ግን በአገልግሎት መበርታት እንዳለብንና ኃላፊነታችንን በፈሪሀ እግዚአብሔር መወጣት እንዳለብን ተስማምተን ተለያየን፡፡ ’’
‘‘እየውልህ አቤል ከማንኛውም አይነት አገልግሎት በፊት ሊታሰብበትና ሊቀድምም የሚገባው ጉዳይ የአገልጋዮች መንፈሳዊነት ነው፡፡’’ ምን ለማለት እንደፈለገ ስላልገባኝ አይኖቼ አፈጠጡበት፡፡እንዴት አድርጎ እነደሚያብራራልኝ እያሰበ ነው መሰለኝ ጥቂት ፋታ ወሰደ፡፡
‘‘መንፈሳዊ አገልግሎት የሚጀምረው መንፈሳዊ ከመሆን ነው፡፡ መንፈሳዊ ሳይሆኑ ማገልገል የጉልበት ስራ ከመስራት በምን ሊለይ ይችላል?’’ አለኝ፡፡ በርግጥ እውነቱን እኮ ነው ስል አሰብኩኝ፡፡ በሦስት አመታት የግቢ ቆይታዬ የነበረኝን የአገልጋይነት ሕይወት በጥልቀት ማሰላሰል ጀመረኩ፡፡ በደስታ ከሰራሁባቸው ቀናት ይልቅ እዳይቀር ያህል ብቻ፤ በድካምና በመሰላቸት የሰራሁባቸው ቀናት ይበልጣሉ፡፡ ችግሮችን የፈታሁባቸው መንገዶች ከመንፈሳዊነታቸው ይልቅ ስጋዊነታቸው ያይላል፡፡
‘‘ምን መሰለህ አቤል ምንም እንኳን የምንጓዝበት የሕይወት መስመር አንድ አይነት ቢሆንም፤ አረማመዳችን ግን የግድ መለያየት አለበት፡፡ ከእኔ የተሻለ መንፈሳዊ ህይወት ቢኖርህ ደስታዬ ነው፡፡ እኔም ግቢ እያለሁ በመንፈሳዊ አገልግሎት ውስጥ በንቃት እሳተፍ ነበር፡፡ ዛሬ ግን እኔም ሆንኩኝ ጓደኞቼ አይደለም ከአገልግሎት ሕይወት ከቤተ ክርስቲያንም ሕይወት እጅግ ብዙ እርቀናል፡፡’’
‘‘እንዴት ታደርገኝ ይሆን? ’’ ትል ነበር አያቴ፡፡ ዛሬ ከሆንኩት ይልቅ ነገ የምሆነው ይበልጥ አሳሰበኝ፡፡ በርግጥ ታላቅ ወንድሜ የሚለኝ ነገር ሁሉ በሕይወቴ በተጨባጭ እየሆነ ያለ ነገር ነበር፡፡ ከአገልግሎቱ መንፈሳዊነት ይልቅ የአገልግሎቱ መቅረት ወይም አለመቅረት ይበልጥ ያሳስበኛል፤ በአገልግሎቱ ከሚጠቀሙት ሰዎች ይልቅ ስለአገልግሎቱ ድምቀትና የሰዎች ቁጥር ይበልጥ እጨነቃለሁ፡፡ 
     ‘‘ስማ አቤል አንድ ነገር ልጠይቅህ ?’’
     ‘‘ይቻላል’’
‘‘የእግዚአብሔር ትልቁ ጉዳይ አገልግሎቱ ነው ወይስ የሚገለገሉት ነፍሳት ’’
‘‘ሁለቱም ይመስለኛል’’
‘‘አይምሰልህ እግዚአብሔር አገልግሎትን የሠጠን ሰዎች ሁሉ እርሱን ወደማወቅ እንዲደርሱና የዘለዓለምን ሕይወት እንዲወርሱ ነው፡፡ ለሰው ልጆች ሁሉ መዳንና መንፈሳዊ እድገት የማይተጋ አገልግሎት እግዚአብሔር ደስ አይሰኝበትም፡፡ ሰዎችና መላእክት የተፈጠሩት እግዚአብሔርን እንዲያገለግሉና ክብሩን እንዲወርሱ እኮ ነው፡፡’’
 ‘‘እና ምን መሆን አለበት እያልከኝ ነው?’’
‘‘መሆን ያለበትማ ከአገልግሎቱ ይበልጥ በአገልግለሎቱ ውስጥ ስለሚኖርህ መንፈሳዊነትና በአገለግሎቱ ስለሚጠቀሙት ሰዎች ነፍስ የበለጠ ተጠንቀቅ፡፡’’
‘‘የምር ግን ብዙ አገልግሎትና ብዙ አገልጋዮች ባሉበት ዘመን የአገልግሎቱ ፍሬ ለምን ጥቂት ሆነ? የሚደከመውንስ ያህል ለምን ለውጥ አይታይም? ’’
‘‘ምክንያቱ ግልፅ ነው አገልጋዮቹ መንፈሳዊነት ይጎድላቸዋል፡፡ ከሰዎች ነፍስ ይልቅ አገልግሎቱን ያሰቀድማሉ፡፡ ልክ ጌታ በመዋዕለ ስጋዌው እንደገሰፃቸው ፈሪሳውያን ከወጭቱ ውስጥ ይልቅ ለውጪው ይበልጥ ይጠነቀቃሉ፡፡መንፈሳዊ ሳልሆን  ያገለገልኩባቸው ብዙ አመታት ዛሬ ላይ እንዴት ይቆጩኛል መሰለህ፡፡ ለዚህም ነው ዛሬ ከትዝታው ባለፈ በድርጊት የሚገለጥ አንዳች ነገር ሊተርፍልኝ ያልቻለው፡፡’’
ታላቅ ወንድሜን በጣም እወደዋልሁ፣ የእርሱ ደግሞ ከእኔም ይለያል፤ ይበልጥ ይወደኛል፡፡ ከማንም በተሻለ ለስሜቴ ቅርብ ነው፡፡ ጥቂት ተናግሬ አብዝቶ ይረዳልኛል፡፡ እኔም ብሆን ልረዳው እሞክራለሁ፡፡ ለዚህም ሳይሆን አይቀርም መንፈሳዊ ሆኖ ስለማገልገል እያወራን በጥልቅ መገናዘብ ውስጥ ገብተን የምንተያየው፡፡ ሊለኝ የፈለገው ገብቶኛል፡፡ ከቃላቱም በላይ በወንድምነቱ ውስጥ ያለው እውነተኛ ስሜት ነገሮችን ይበልጥ እንድረዳቸው ያደርገኛል፡፡ …………. በመካከላችን ዝምታ ሰፈነ፡፡ሁለታችንም ግን ለየራሳችን በውስጣችን እያወራን ነበር፡፡ ውስጥን ዘልቆ የሚያይ ያህል በጥልቅ ስሜት አተኩሮ ተመለከተኝ፡፡ ሊለኝ የፈለገው ግን ገብቶኝ ነበር፡፡
እጁን ወደ ራስጌዬ ልኮ መፅሐፍ ቅዱስ አነሳ፡፡ ‘‘እንካ እስኪ ይህንን አንብብ’’ የማነበውን በጣቱ እያመለከተኝ፡- የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ነበር ለሮሜ ሰዎች የጻፈላቸው ምዕራፍ 2 ከቁጥር 07-@4 በጥልቅ መገረም ውስጥ ሆኜ እንዲህ አነበብኩት ፡-
‘‘አንተ ግን አይሁዳዊ ብትባል በህግም ብትደገፍ ፣ በእግዚአብሔርም ብትመካ፣ ፈቃዱንም ብታውቅ  ከህግም ተምረህ የሚሻለውን ፈትነህ ብትወድ በህግም የእውቀትና የእውነት መልክ ስላለህ፣ የእውሮች መሪ፣ በጨለማም ላሉ ብርሀን፣ የሰነፎችም አስተማሪ፣ የሕፃናትም መምህር እነደሆንህ በራስህ ብትታመን ፤ እንግዲህ አንተ ሌላውን የምታስተምር ራስህን አታስተምርምን? አትስረቅ ብለህ የምትሰብክ ትሰርቃለህን? አታመንዝር የምትል ታመነዝራለህን? ጣዖትን የምትጸየፍ ቤተ መቅደስን ትዘርፋለህን? በህግ የምትመካ ህግን በመተላለፍ እግዚአብሔርን ታሳፍራለህን? በእናንተ ሰበብ የእግዚአብሔር ስም በአህዛብ መካከል ይሰደባልና ተብሎ እንደተፃፈ፡፡ ’’
ከዚህ በኋላ ለረጅም ጊዜ ምንም አልተነጋገርንም፡፡ ሁለታችንም በየራሳችን ጥልቅ ስሜት ውስጥ ሰጥመን ነበር፡፡ ከራሳችን ጋር ለየራሳችን እያወራን ብዙ አሰላሰልን፤ እማዬ ከለቅሶ ቤት ተመልሳ ከየሄድንበት እረጅም የሀሳብ መንገድ እስክትመልሰን ድረስ፡፡
‘‘ውይ አቤልዬ መጥተሀል እንዴ?’’ ሁለታችንም ተነስተን ቆምን፡፡ ‘‘እስኪ ና ሳመኝ ጌታዬ’’
የእናቴ ነገር ሁሌም ይገርመኛል፡፡ ባገኘችኝ ቁጥር እንደ አዲስ ትናፍቀኛለች፡፡ ለአንድ ቀን አዳር ተለያይተን የአመታት ናፍቆት ያህል እንቅ አድርጋ ትስመኛለች፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቴክኖሎጂ ኢኒስቲቲዩት የሶስተኛ አመት የኤሌክትሪካል ምሕንድስና ተማሪ ነኝ፡፡ በየሳምንቱ አርብ ማታ ወደ ቤቴ እየመጣሁ ከእናቴና ከወንድሜ ጋር እሁድና ቅዳሜን አሳልፋለሁ፡፡ አባቴና እናቴ አብረው አይደለም የሚኖሩት፡፡ ለምን እንደተለያዩ አናውቅም፤ እናታችንንም ምክንያቱን አልጠየቅናትም ፡፡ አባታችን እናታችንን አይረዳትም፡፡ ወጪያችንን በሙሉ እናታችን ብቻዋን ትሸፍናለች፡፡ አሁን እንኳን ታላቅ ወንድሜ አልዓዛር ስራ ስለያዘ በወጪ ያግዛታል፡፡ አባታችን አልፎ አልፎ እየመጣ ይጠይቀናል፡፡ እናታችን አንድም ቀን ስለአባታችን ክፉ ተናግራ አታውቅም፡፡ ስምረት እኔንና አልዓዛርን ያሳደገችን ሞግዚታችን ናት፡፡ የማታ ትምህርት እየተማረች ዘጠነኛ ክፍል ደርሳለች፡፡ ከእናታችን ጋር የእህትማማቾች ያህል ይግባባሉ፡፡
     ‘‘አልዓዛርዬ አንተስ ለምን ይቅርብህ ና እስኪ ልሳምህ፡፡ ከአንተም ጋር ቢሆን አብረን አልዋልን’’ ብላ በስስትና በናፍቆት እቅፍ አድርጋ ሳመችው፡፡
       ‘‘እማዬ ዛሬ ለራት ምን ሰርተሽ ጠበቅሽኝ?’’ አልኳት፡፡
        ‘‘ያቺን የምትወዳትን ድፍን ምስር በቅመም አሳምሬ ሰርቼልሀለሁ፡፡ እራት ይቅረብ አይደል?’’ እራት ልታቀርብ ወጥታ ሔደች፡፡
እናታችን ሲበዛ የፍቅር ሰው ናት፡፡ ለሌሎች ደስታ ስትል የኔ የምትለውን ሁሉ የምትተው፣ ማንንም ስለድካሙ የማትወቅስ፣ የበጎ ነገር ሁሉ ምሳሌያችን ናት፡፡ እንዲያውም አልዓዛር     ‘‘ፍቅር የሚሰጥ መሆኑን የተማርኩት ከእናቴ ነው፡፡’’ ይላል፡፡ እውነቱን ነው ከእናታችን ያገኘነው ፍቅር ብዙዎችን እስክንወድበት ድረስ በዝቶልን ተመልክቻለሁ፡፡
       ‘‘ ስማ አቤል ’’
      ‘‘አቤት አልዓዛር  ’’
      ‘‘ለእኔ ሃይማኖትን ማን እዳስተማረኝ ታውቃልህ?’’ አልመለስኩለትም ነበር፡፡ የሚለኝን ለመስማት ጓጉቼ ዝምታን መረጥሁ፡፡
      ‘‘ ማን ይመስልሃል ?’’
       ‘‘ለመጀመሪያ ጊዜ ቃለ እግዚአብሔርን ያስተማሩህ ሰዎች ናቸዋ፡፡’’ እራሱን በአሉታ ነቀነቀ፡፡ ማን ሊሆን ይችላል ብዬ አሰብኩ፡፡
       ‘‘ለእኔ ሃይማኖትን  ያስተማረችኝ እናቴ ናት’’
      ‘‘አልገባኝም ’’
     ‘‘ እስኪ ተመልከት እማዬ አንድም ቀን ስታማርር ሰምተሃት ታውቃለህ? አታውቅም፡፡ በነገር ሁሉ እግዚአብሔርን ታመሰግናለች፡፡ ይህ ማለት ግን ምንም ችግር ገጥሟት አያውቅም ማለት አይደለም፡፡ እኛን ስታሳድግ ብዙ ልትቸገር ትችላለች፡፡ ስለአባታችንም ቢሆን አንድም ቀን ክፉ ስታወራ ሰምተን አናውቅም፡፡ እኔና አንተ ከተማርነው የሃይማኖት ትምህርትና እማዬ ከተማረችው የትኛው በደንብ የተጠናና የተደራጀ ይመስልሃል?’’ ጥልቅ በሆነ ስሜት ለደቂቃዎች ያህል ተመለከተኝ፡፡ እኔም ብሆን ለመልስ አልቸኮልኩም፤ የእናቴን ክርስቲያናዊ ሕይወት ከእኛ ከልጆቿ ክርስቲያናዊ ሕይወት ጋር እያወዳደርኩ ነበር፡፡ በእርግጥ እናታችን የእኛን ያህል በደንብ የተደራጀ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት የተማረችበትን ጊዜ አላስታውስም ሆኖም ከእኛ ይልቅ እርሷ በተግባር የተገለጠና የሚታይ ክርስቲያናዊ ሕይወት አላት፡፡ መልሴ ስለዘገየበት የጥያቄውን መልስ ከነማብራሪያው እንዲህ ሲል ቀጠለ ፡-
‘‘አየህ አቤል ስለሃይማኖት ትምህርት ከሆነ እማዬ ከእኛ ጋር ሊነፃፀር የሚችል ትምህርት የላትም፤ የእኛን ያህል የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት በደንብ በተደራጀ መልኩ አልተማረችም፤ ሆኖም ግን ከእኛ ጋር ሊነፃፀር በማይችል መልኩ በተግባር የተገለጠ ክርስቲያናዊ ሕይወት አላት፡፡ የበደሏትን ሳይቀር ትወዳለች፣ሁልጊዜ ለበጎ ነገር ትተጋለች፣ የተቸገሩትን ትረዳለች፣ ባወቀችው ለመኖር ትጥራለች፣ ዘወትር በጸሎት ትተጋለች፣ ለችግሮቿ ሁሉ እግዚአብሔር መፍትሄ እንዳለው ታምናለች፣ እርሱንም ብቻ በትዕግስት ትጠብቃለች፣ በሀዘኗም ሆነ በደስታዋ እግዚአብሔርን ታመሰግናለች….. ስለሆነም ከእኔና ከአንተ ይልቅ እማዬ ክርስቲያን ነች፡፡ እኔና አንተስ? ልንኖረው የሚገባንን ህይወት ታሳቢ ባደረገ መልኩ ስርዐተ ትምህርት ተቀርጾልን በተደራጀ መልኩ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ቃለ እግዚአብሔር ተምረናል፣ ብዙ መንፈሳዊ መፃህፍትን አንብበናል፣ ስለቤተ ክርስቲያን ሕይወት ብዙ ተምረናል ግን ደግሞ በተማርነው ልክ አንኖርም፣ ከመማር ባሻገር የተማርነውን ለመተግበርና በኑሯችን ለመግለጥ አንጥርም … ስለሆነም አይደለም የተማርነውን ያህል የእማዬን ያህል እንኳን ክርስቲያኖች መሆን አልቻልንም፡፡’’
እውነቱን ነው፡፡ ከማወቅ ባለፈ በተግባር የተገለጠ ክርስትና እንዲኖረኝ አልተጋሁም፡፡ በመማሬና በማወቄ ውስጥ ያመጣሁትን ብልጫ ፈለግሁት፣ በእርግጠም አንዳችም ብልጫ አልነበረኝም፡፡ አስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ስለመማር እንጂ በተማርሁትና በተረዳሁት በጥቂቱ እንኳን ለመኖር አለማሰቤ በጣም ቆጨኝ፡፡
‘‘ምን መሰለህ የምንማረውና የምናውቀው እንደተማርነው ለማድረግና ለመኖር ካለሆነ በመማርና ባለመማር መካከል ልዩነቱ ምን ላይ ነው? ቅዱስ ጴጥሮስም ‘የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሏል’ ያለው ይህንን ነው፡፡ 1ኛ ጴጥ 2፣21፡፡ ክርስቶስ የተወልን ፍለጋ ደግሞ አውቀን ብቻ የምንተወው ሳይሆን እንዳወቅነውና እንደተረዳነው መጠን በተግባር የምንታዘዘውና የምንኖረው ነው፡፡’’
‘‘በምትለው ነገር እኮ ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ፤ ግን ችግሩ የቱ ጋር እንዳለ ነው ማወቅ የምፈልገው፡፡ ከእውቀት ባለፈ በተግባር የተገለጠ ሕይወት እንዳይኖረን ያደረገን ችግር የቱ ጋር እንዳለ እንድታሳየኝ እፈልጋለሁ፡፡’’
‘‘ በእርግጥ ችግሩ አንድ ቦታ ብቻ ስለማይሆን በአጭሩ እንዲህ ነው ብሎ መመለስ አይቻል ይሆናል፡፡ ሆኖም በተግባር ለተገለጠ ክርስትና ተገቢውን ትኩረት አለመስጠታችንና ከልጅነታችን አንስቶ ቀስ በቀስ እያደግንበትና እየተለማመድነው እንድንመጣ አለመደረጋችን ለዛሬ ችግራችን  አስተዋፅዖ ሊኖራቸው እንደሚችል ግን አስባለሁ፡፡’’
…….. ይቀጥላል ……

ስለ ቤተ ክርስቲያናችን እንወቅ



ስለ ቤተ ክርስቲያናችን እንወቅ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ የክርስቶስ መንግስት እንደራሴ፣ የመንግስቱ ወንጌል አገልጋይ፣ ለሰው ልጆች ሁሉ መዳን የምትሠራና የምትተጋ፣ የክርስቶስ አካሉ የምትሆን የተቀደሰች ጉባኤ ናት፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን ራስ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የክርስቶስ አካሉ ናት፡፡ ቆላ 1፣18፡፡ እኛ ደግሞ የክርስቶስ የአካሉ ብልቶች ነን፡፡ ኤፌ 5፣19፡፡ ስለሆነም ስለመዳን ስናስብ በዚህ ኅብረትና አንድነት ውስጥ ሆነን ነው፡፡ አካሉ ከምትሆን ቤተ ክርስቲያን የተለዩ ብልቶች ራሷ ከሆነው ከኢየሱስ ክርስቶስም ስለሚለዩ መዳን አይቻላቸውም፡፡ ስለሆነም በቤተ ክርስቲያን ኅብረትና አንድነት ውስጥ የሚኖረን ሱታፌ የመዳናችን መንገድ ነው፡፡ ራስ፣ አካልና የአካል ክፍሎች ተለያይተው መኖር እንደማይችሉ ሁሉ ያለ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ልትኖር አትችልም፤ ያለቤተ ክርስቲያንም ምእመናን ሊኖሩ አይችሉም፡፡ በዚህም የተነሳ ስለ ሰው ልጆች መዳን ስናስብ የሰው ልጆች በቤተ ክርስቲያን ምስጢራት ውስጥ የሚኖራቸው ሱታፌ ወሳኝ ነው የምንለው ስለዚህ ነው፡፡ የአካል ክፍሎች ብቻቸውን፣ ራሳቸውን ችለው በራሳቸው ሕይወት ሊኖራቸው እንደማይችል ሁሉ፣ የክርስቶስ አካሉ ከምትሆን ከተቀደሰችው ጉባኤ ከቤተ ክርስቲያን ኅብረትና አንድነት የተለዩ ነፍሳትም መዳናቸውን መፈጸም አይቻላቸውም፡፡ እናም ስለቤተ ክርስቲያን የምናምነው እምነትና የምናውቀው እውቀት በመዳን መንገድ ላይ ወሳኝ ነው፡፡
ስለ ቤተ ክርስቲያን ማውቅ ያለብን ምንድን ነው?
ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ደም የተዋጀች የራሱ የእግዚአብሔር ገንዘብ ናት፡፡ ሐዋ 2፣28፡፡ ትምህርቷ፣ ስብከቷና ፍለጋዋ ሁሉ ከክርስቶስ ያየችውና የተማረችው ነው፡፡ የክርስቶስ ከሆነው በቀር የራሷ የምትለው አንዳችም ነገር የላትም፡፡ “የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሏልና፡፡” 1ኛ ጴጥ 2 ፣21 ፡፡ ቤተ ክርስቲያን መምህሯ አንድ እርሱም ደግሞ ክርስቶስ ነው ማቴ 23፣8፡፡ “ከእኔ ተማሩ”  ማቴ 11፣29 ተብለናልና ከክርስቶስ ያልተማርነው ማናቸውም አይነት እንግዳ ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተቀባይነት የለውም፡፡ የሰማይ መልአክ እንኳን ቢሆን ክርስቶስ ካሳየንና ካስተማረን ትምህርት የተለየ እንግዳ ትምህርት ቢያሳየንና ቢያስተምረን ቤተ ክርስቲያን አትቀበለውም፡፡ “ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ ይሁን” ተብሏልና እንደ ክርስቶስ ትምህርት ያለሆነ ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ስፍራ የለውም፡፡ ገላ 1፣8፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሚመጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም ብላ ታምናለች፡፡ 2ኛ ዮሐ 1፣9፡፡ ስለሆነም ስለ ቤተ ክርስቲያን ልናወቀው የሚገባን መሰረታዊ ነገር ከክርስቶስ ያየችውንና የተማረችውን ትምህርት ነው፡፡ ይህም ደግሞ ስለመዳን፣ ስለ ዘላለማዊ ሕይወት፣ ስለ ጽድቅና ፍርድ የምታምነውና የምታስተምረው ትምህርት ነው፡፡ “እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው፥ መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው” ሮሜ 1፣ 17 ተብሎ ተጽፏልና ለማመን የእግዚአብሔርን ቃል መስማትና መማር ያስፈልጋል፡፡
የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ለማወቅ ምን እናድርግ?
ሀ. የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመደበኛነት ጊዜ መድበን እንማር፡- በአሁኑ ጊዜ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመደበኛ ሁኔታ ጊዜ መድበው የሚያስተምሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ኮሌጆች፣ የተለያዩ ግቢ ጉባኤያት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና የሰርክ ጉባኤያት ስላሉ ጊዜ መድበን እንማር፡፡ ካልተማርን የእግዚአብሔር ሐሳቡና ምክሩ እንዴት ሊገባን ይችላል? ስለመዳንና ስለዘለዓለም ሕይወትስ እንዴት ልንረዳ እንችላለን? ከመደበኛ ትምህርቶቹ በተጨማሪም የርቀት ትምህርት መርሐግብር ያላቸው መንፈሳዊ ኮሌጆችና ሰንበት ትምህርት ቤቶችም ስላሉ በአካል መገኘትና መማር የማንችል ባለንበት ቦታ ሆነን በርቀት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት መማር እንችላለን፡፡ እዚህ ጋር ሊጤን የሚያስፈልገው ጉዳይ ቢኖር ስንማር የሚያስተምሩን አካላት ትክክለኛ የቤተ ክርስቲያን መምህራን መሆናቸውንና ሕጋዊውን የቤተ ክርስቲያን መዋቅር ተከትለው የሚሠሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይጠበቅብናል፡፡ የቤተ ክርስቲያናችንን መምህራን የሚመስሉና ነን የሚሉ፣ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያናችን የማታውቃቸው፣ የማታስተምረውን ትምህርት የሚያስተምሩ አካላት ስላሉ አስቀድሞ መጠንቀቁና ነገሮችን በንቃት መከታታሉ ለሁሉም ነገር ጠቃሚ ነው፡፡ ለነፍሳችን ድኅነት ብለን ያደረግነው ምናልባት ለጥፋቷ እንዳይሆን መጠንቀቅ ያሻል፤ ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና፡፡  ኤፌ 5፣16
ለ.  እንጸልይ፡- የጸሎት ሕይወት በመንፈሳዊ ሕይወታችን ለሚኖረን ሁሉን አቀፍ እድገትና ለውጥ ጉልህ ድርሻ አለው፡፡ ስንጸልይ ምስጢር ይገለጥልናል፣ የራቀው ይቀርብልናል፣ የረቀቀው ይከሰትልናል፣ ወደ ቀናው መንገድ ይመራናል፡፡ በአጠቃላይ የእግዚአብሔር ሐሳብና ምክር በሕይወታችን ውስጥ የተገለጠና የተረዳ ይሆንልናል፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር፥ ልመናና ጸሎት፣ ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ፡፡ ሰዎች ዅሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኀኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሠኝ ይህ ነው።” 1ኛ ጢሞ 2፣1-4፡፡ የጸሎት ሕይወት የሌለው ሰው መቼም ቢሆን እውነትን ወደማወቅ ሊደርስ አይችልም፡፡
. እናንብብ፡- መንፈሳውያት መጻሕፍት በእግዚአብሔር ፊት የምናድግባቸው መልካም መንገዶች ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያናችንንና የቅዱሳን አባቶቻችንን ትምህርት በደንብ ልናውቅና ልንረዳ የምንችለው በመንፈስ ቅዱስ የጻፏቸውን ቅዱሳት መጻሕፍቶቻቸውን ማንበብ ስንችል ነው፡፡ “ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል፡፡” 2ኛ ጢሞ 3፣15 እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳውያት መጻሕፍት መዳን የሚገኝበትን ጥበብ የሚሰጡ ናቸው፡፡ መንፈሳውያት መጻሕፍት በስጋዊ ሐሳብና ፈቃድ የተጻፉ ሳይሆኑ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምክርና ፈቃድ የተጻፉ ስለሆኑ ለመንፈሳዊ ሕይወት እድገትና ለመዳን እጅግ ጠቃሚዎች ናቸው፡፡ “ይህን በመዠመሪያ ዕወቁ፤ በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ዅሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም፤ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ።” 2ኛ ጴጥ 1፣2-21 ተብሎ እንደተጻፈ በቅዱሳት መጻሕፍት ያለው ሁሉ የመንፈስ ቅዱስ ምክርና ሐሳብ እንደሆነ እናምናለንና ለመንፈሳዊ ሕይወታችንና ለመዳናችን የሚጠቅም መሆኑን እንቀበላለን፡፡ በተለይም በአሁኑ ወቅት በየሞባይሎቻችንና በየኮምፒውተሮቻችን ላይ ማንበብ ስለምንችልና መጽሓፍትንም በለስላሳ ቅጂ (soft copy) በቀላሉ ማግኘት ስለምንችል በቀላሉ እውነቱን ወደ ማወቅ  እንደርሳለን፡፡
መ. እንጠይቅ፡- ‘‘አባትህን ጠይቅ ያስታውቅህማል፤ ሽማግሌዎችህን ጠይቅ፥ ይነግሩህማል።’’ እንዲል መጠየቅ ስንችል እውነተኛውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት መለየትና መረዳት እንችላለን፡፡ ዘዳ 32፣7፡፡ በእርግጥ የምንጠይቃቸው ሰዎች እውነተኞች የቤተ ክርስቲያናችን አባቶችና መምህራን ከሆኑ ለሕይወታችን የሚረባንን፣ የሚበጀንንና መዳን የሚገኝበትን ጥበብ እናገኝበታለን፡፡
. ትሕትናን ገንዘብ እናድርግ፡- ‘‘በትሑታን ዘንድ ግን ጥበብ ትገኛለች።’’ እንዲል መጽሐፍ ትሑታን ስንሆን እግዚአብሔር አምላካችን ምስጢሩንና ጥበቡን ይገልጥልናል፡፡ ምሳ 11፣2፡፡ እግዚአብሔር የትሑታን አምላክ ነውና ስለትሕትናችን ሲል ጸጋውን ያበዛልናል፣ ትዕቢተኞች ብንሆን ግን ጸጋው ትርቅብናለች፡፡ ‘‘በፌዘኞች እርሱ ያፌዛል፣ ለትሑታን ግን ሞገስን ይሰጣል፡፡’’ ተብሎ ተጽፏልና ምሳ 3፣34፡፡
ረ. በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንሳተፍ፡- ቤተክርስቲያናችን የአገልግሎት ቤት ናት፡፡ ማኅሌቱ፣ ሰአታቱ፣ ቅዳሴው፣ ጉባኤው፣ የሰበካ ጉባኤና የሰንበት ትምህርት ቤት አገልግሎቱ፣ ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደቱ ሁሉ ለእኛ ስለሆነ በምንችለው መሳተፍ አለብን፡፡ ከመንፈሳዊ አገልግሎት የተለየ ሰው በመንፈሳዊ ሕይወት ሊያድግ አይችልም፡፡ አገልግሎት ትልቅ ትምህርት ቤት ነውና ስናገለግል ብዙ እንማራለን፡፡ የተማርነውን ስንተገብረው ይበልጥ ይዋሓደናል፡፡ የማወቅ ዓላማው ለመተግበር ስለሆነ አገልግሎት ወደ ማወቅና ወደማድረግም የሚያደርሰን መንገድ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና›› እንዳለ በእግዚአብሔር መንግሥት አብረን እንሥራ፣ የእግዚአብሔር ስራ ለሌሎች ብቻ የምንተወው ሳይሆን እኛም የምናሳተፍበት የክርስትናችን ድርሻ ነው፡፡ (2ቆሮ 1፤24፣ቆላ 4፤11)፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አምላከ አበዊነ፡፡

ነገረ ክርስቶስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
ነገረ ክርስቶስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
   እንዲህ እናምናለን፤ እንዲህም እናስተምራለን፡፡ (ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ)፡፡
ነገረ ክርስቶስ ማለት ስለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምናምነውን እምነት የምናስተምረውን ትምህርት የሚያጠቃልል ነው፡፡ ይህ ክፍለ ትምህርት በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ስለ ጌታችን መድኃኒታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚታመነው፣ የሚነገረው፣ የምንመራበት ምንድነው የሚለውን በሚገባ ለመረዳት በቅዱሳት መጻሕፍት፣ በሊቃውንት፣ በትውፊት የተላለፈውን አስተምህሮ የምናቀርብበት ነው፡፡
   አግዚአብሔር አምላካችን የሚታየውን ዓለም ከማስገኘቱ በፊት እስከ ዘላለም ድረስ በአንድነቱና በሦስትነቱ፣ በመለኮቱ፣ በመንግሥቱ አለ፡፡ ከጎሕና ከጽባሕ በፊት፣ ከመዓልትና ከሌሊት በፊት፣ መላእክት ሳይፈጠሩ እግዚአብሔር አለ፡፡ ሰማያት ሳይዘረጉ፣ የየብስም ፊት ሳይታይ፣ ሐመልማላት ሳይበቅሉ እግዚአብሔር በመንግሥቱ ነበረ፡፡ ከሚንቀሳቀስ እንስሳ በፊት ከሚበሩም አዕዋፍ በፊት፣ ከባሕር አራዊት በፊት፣ እግዚአብሔር በመንግስቱ ነበረ፡፡ አዳምን በእርሱ አምሳልና አርአያ ሳይፈጥረው፣ ትእዛዙንም ሳያፈርስ እግዚአብሔር በመንግሥቱ ነበረ (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ)፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው ወወልደ ማርያም ሥግው ከአምላክ የተገኘ አምላክ፣ ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከባሕርይ የተገኘ ባሕርይ፣ ከሕይወት የተገኘ አዳኝ ከመድኃኒት የተገኘ መድኅን፣ ከገዥ የተገኘ ገዢ፣ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ ህላዌ እንደሆነ እናምናለን (መዝገበ ሃይማኖት)፡፡
ከአብ መወለዱም በዚህ ዘመን፣ በዚህ ወቅት፣ በዚህ ሰዓት ተብሎ ዘመን አይቆጠርለትም፤ በሰውና በመላእክት አእምሮም ሊመረመር አይችልም፡፡ ሰውንም ስለማዳን በአባቱ ፈቃድ በእርሱም ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ከቅድስት ድንግል ማርያም ያለ ወንድ ዘር በድንግልና ተወለደ፡፡ ከወለደችውም በኋላ ድንግልናዋ አልተለወጠም፡፡ በሚያስደንቅ ትሕትና ሰው ሆነ፤ በሚያስደንቅ ዙፋኑ ለደቀመዛሙርቱ ሲያገለግል ባዩት ጊዜ አገልጋዮች መላእክት ደነገጡ፡፡ ትሕትና ወዳለበት ፍቅር የአሕዛብን እግረ ልቡና ያቀና ዘንድ ግሩም እሳት በትሕትና መገለጡን ባዩ ጊዜ መላእክት ደነገጡ (ሃይማኖተ አበው ዘያዕቆብ ዘስሩግ)፡፡ ፍጥረቱን ሁሉ ሰብስቦ የያዘና ፍጥረቱን ሁሉ የሚመግብ ጌታቸው በብብቷ (በክንዷ) ተቀምጦ ጡቷን ሲጠባ ባዩ ጊዜ በአርያም ፈለጉና በዚህ ዓለም እንደ ቀድሞው ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አገኙት፡፡ የጌታን ትሕትና ባዩ ጊዜም ዓይኖቻቸውን ወደ ላይ ወደ አርያም ከፍ ከፍ አደረጉ ክንፋቸውንም ዘርግተው ለሁሉ ጌታ ለአንተ ምስጋና ይገባሃል እያሉ ጌታቸውን አመሰገኑ፡፡ (አንቀጸ ብርሃን)
አዳምን ካልታረሰች መሬት የፈጠረው ሔዋንንም ከአዳም ያለእናት የፈጠራት እርሱ ከንጽሕት ድንግል ያለ ወንድ ዘር ተወለደ፡፡ ያለ እናት ሔዋን ተገኝታ ነበርና ስለዚህ የአዳምን ብድራት ትከፍለው ዘንድ አዳም ያለ እናት ሔዋንን ስላስገኘ እንዳይመካ ድንግል ያለ አባት ክርስቶስን ወለደች ይህም ድንቅ በሚሆን አንድነት የፍጥረት ሁሉ እኩልነት ይታወቅ ዘንድ ነው፡፡ (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)፡፡
ዳግመኛም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‹‹ከአዳም አጥንት ጎድን ሲነሳ ምንም አካል እንዳልጎደለው እንዲሁ ከድንግል የምትናገር ነፍስን ሲነሳ ማኅተመ ድንግልናዋ አልተለወጠም፡፡ አዳም የጎድን አጥንት ከእርሱ ከተነሳ በኋላ አካል ሳይጎድለው ፍጹም ሆኖ እንደኖረ እንዲሁ ድንግልም ሕጻን ክርስቶስ ከእርሷ ከተወለደ በኋላ በድንግልና ጸንታ ኖረች›› አለ፡፡ ሕዝ 44፤1-3፣ መኃ 4፤12
ነቢያት ስለእርሱ ሰው መሆን ተነበዩ፡፡ ኢሳይያስ ‹‹እነሆ ድንግል ትጸንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ይሉታል ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው›› አለ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል። ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግሥቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፥ ለሰላሙም ፍፃሜ የለውም። የእግዚአብሔር ቅንዓት ይህን ያደርጋል።›› በማለት ትንቢት ተናገረ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ሕፃኑ አባቱንና እናቱን መጥራት ሳያውቅ የደማስቆን ሀብትና የሰማርያን ምርኮ በአሦር ንጉሥ ፊት ይወስዳልና ስሙን፦ ምርኮ ፈጠነ፥ ብዝበዛ ቸኰለ ብለህ ጥራው አለኝ›› አለ፡፡  (ኢሳ 14 ፣ 9፤6፣ 8፤4)፡፡ ጌታችን በመወለዱ በዲያብሎስ የተያዙትን ማርኳል፣ ሲኦልን በዝብዟልና ስሙ ‹‹ምርኮ ፈጠነ ብዝበዛም ቸኮለ›› ተብሎ ተጠራ፡፡    
የማይደፈር ግሩም ነው፤ በእኛ ዘንድ ግን ትሑት ነው፡፡ የማይደረስበት ልዑል ነው፤ በእኛ ዘንድ ግን የባርያውን መልክ ነሳ፡፡ የማይዳሰስ እሳት ነው፡፡ እኛ ግን አየነው፣ ዳሰስነው፣ ከእርሱም ጋር በላን ጠጣንም (ቅዳሴ ማርያም)፡፡ ሁሉ በእርሱ የተፈጠረና ሁሉን ሚመግብ ሁሉ በእጁ የተያዘ መላእክት የሚታዘዙለትና የሚያገለግሉት፣ እኔ ግን በመካከላችሁ እንደሚያገለግል ነኝ አለ (ሉቃ 22፤27)፡፡
በአዳም ምክንያት የጨለመውን ልቡናችንን ለማብራትና በእርሱ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር ብርሃን ሆኖ የመጣ (ዮሐ 12፤16)፡፡ ጨለማን ያስወገደ ብርሃን የሃይማኖትና የጽድቅ ጣሪያዋ (ጠፈሯ)፣ ሃይማኖትም ወንጌልም፣ በብዙ ድካም እርሱን ደስ ያሰኙት የሚወርሱት፣ የሃይማኖት ገንዘብን ይዘው በሠርክ የሚገቡበት መንግስተ ሰማያት እርሱ ነው (ሉቃ 17፤21 ፣ መልክአ ኢየሱስ)፡፡
ክብርና ምስጋና ይግባውና የእኛን ሞት ሞቶ የእርሱን ሕይወት የሰጠን፡፡ ድዳ ለነበሩት ቃል፣ ለተሰበሩት ምርጉዝ፣ ለዕውራን ብርሃን፣ለሐንካሶች መሄጃ፣ ለለምጻሞች የሚያነጻቸው ሆነ፡፡ በዴዌ የተያዙትን አዳነ፣ ደንቆሮዎችን ፈወሰ፣ ሞትን ዘለፈው ጨለማንም አሰቃየው፡፡ ብርሃን ኅልፈት የሌለበት፣ ፀሐይ፣ የማይጠፋ ፋኖስ፣ በቅዱሳን ላይ ዘወትር የሚያበራ ፀሐይ፣ በተወሰነ በቁርጥ ፈቃድ ለዓለም ጌጥ ሁሉን የፈጠረ፣ ሰውን ለማዳን ለሁሉ የተገለጠ፣ ነፍሳችንን የመለሳት እርሱ ነው (ኪዳን ዘነግህ)፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‹‹ምንስ እላለሁ ምንስ እናገራለሁ ከዘመን በፊት የነበረ እርሱ ትንሽ ሕጻን ሆኗልና ፈጽሜ አደንቃለሁ፡፡ ከሰማየ ሰማያት በላይ የሚሆን በዘለዓለማዊ ዙፋን የሚኖር እርሱ በበረት ተጣለ›› በማለት የጌታን ትሕትና አደነቀ፡፡  ነፋሳት የሚታዘዙለት፣ መላእክት የሚላላኩት እርሱ ለእናቱና ለዘመዶቹ እየታዘዘ አደገ፡፡ ሁሉን አዋቂ ሲሆን አልአዓዛርን የት ቀበራችሁት ብሎ ጠየቀ፤ እርሱ የሕይወት ውሃ ሲሆን ከሳምራዊት ሴት ውሃ ለመነ፡፡ ምራቅ ከጭቃ ጋር ለውሶ እውር ያበራ እርሱን አይሁድ ምራቅ ተፉበት፡፡
ጠባቂ አጥተው ለባዘኑት መልካም እረኛ ሆኖ መጣ ስለበጎቹም ነፍሱን ሰጠ፡፡ (ዮሐ 1፤11) ቅዱስ ያሬድ ‹‹ኖላዊ ኄር ኖላዊሆሙ ለእስራኤል ዘመጽአ ውስተ ዓለም ተአዛዚ ከዊኖ ክርስቶስ ለአሕዛብ፡፡ ኦሆ ብሂሎ ተአዛዚ ከዊኖ ወረደ ወመጽአ ለአድኅኖ… ከመ ይቤዙ ወያድኅን ዓለመ፡፡ ቸር እረኛ እስራኤልን የሚጠብቃቸው ታዛዥ ሆነ ክርስቶስ ለአሕዛብ የመጣ፡፡ እሺ ብሎ ታዛዥ ሆኖ ዓለምን ይቤዥና ያድን ዘንድ ከሰማይ ወረደ፤ መጣ፡፡›› (ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ ገጽ )*)፡፡ በማለት ሁሉን የሚገዛ አምላክ ዓለሙን ሊቤዥና ሊያድን እሺ ብሎ በፈቃዱ መምጣቱን መሰከረ፡፡
ሁሉን የሚመግብ፣ የሕይወት እንጀራንና የሕይወት መጠጥን የሚሰጥ ጌታ ወደ ሰርግ ተጠራ፡፡ ለፍጥረቱ ማዕድን የሚያዘጋጅ ጌታ በፈሪሳዊው ስምዖን ቤት ለግብዣ ተጠራ፡፡ ዮሐ 2፤2፣ ሉቃ ፤36-37፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በፈሪሳዊው ማዕድ ላይ የቀረበው የጌታ ማዕድ በሚለው ስብከቱ ‹‹ ንስሓ ስለምትገባው ስለዚያች ኃጢአተኛ ሴት ሲል ከግብዣው ቤት ተገኘ፤ ጌታ ርሀቡ ሥጋዊው ምግብ ሳይሆን የዚያች ኃጢአተኛ እንባ እንጂ… ወደ ፈሪሳዊው ስምዖን ቤት የሄደው በምግብና በመጠጥ ለመዝናናት አልነበረም ሕይወት መድኃኒት የሆነውን ትምህርቱን በማዕዱ ለማቅረብ በመሻቱ ነበር እንጂ፡፡ … ክፉ የተባለው ሰይጣን በመብል ምክንያት አዳምና ሔዋንን ሞትን የሚያመጣ ምክርን እንደመከራቸው እንዲሁ ቸሩ ጌታችን ደግሞ በማዕድ ቦታ ተገኝቶ ሕይወት ሰጪ የሆነ ትምህርቱን ለአዳም ልጆች በማዕዱ አቀረበ፡፡ እርሱ ጌታችን የጠፉትን ነፍሳት ለማጥመድ አሳ አስጋሪ ነበር፡፡ ቀራጮችና አመንዝሮች ወደ ስካርና ሥርዐት አልበኝነት ሲፋጠኑ ተመለከታቸው፤ ሥጋንም ከሚያወፍር የማዕድ ቦታ እነርሱን በማስገር ነፍስን ወደሚያወፍር ጾም ሊያሻግራቸው የቃሉን መረብ በማዕዱ ውቅያኖስ ላይ ጣለው፡፡›› በማለት ገለጸው፡፡ (ስብከት ወተግሳጽ ዘቅዱስ ኤፍሬም)፡፡
ይቀጥላል….