የአማልክት አምላክ፤ የአጋዕዝት ጌታ አቤቱ ወደአንተ አነዋወሩ የማይፈጸም ኅቡእ አምላክ፤ ከሁሉ ይልቅ ልዑል ነው፤
አነዋወሩ የማይገኝ ነው፡፡
የሚያቃጥል እሳት፣ የሚያድንም እሳት፣ የአማልክት አምላክ፣ የጌቶችም ጌታ ነው፡፡ ዙፋኑ ከሰማያት
በላይ፤ የእግሩም መመላለሻ ምድር ነው፡፡ በብርሃን የሚኖር ልዑል
ምጡቅ ነው፡፡
በሰማይ ያለ ማደሪያው ሥውር ልዑል ነው፡፡ የእሳት መጐናፀፊያ የሚጐናፀፍ በነደ እሳትም ያጌጠ ነው፡፡ ዙፋኑ ከእሳት
አለቆች በላይ የሚሆን፤ መመላለሻው በማይዳሰስ በአየር ላይ፣ ጠፈሩም በልዑል ሰማይ፣ መንኰራኩሩ ደመና፣ ጎዳናውም በባሕር ማዕበል
ላይ፣ በሚላኩት በእሳት አለቆችም ነው፡፡
የሚያቃጥል እሳት እንዳያቃጥላቸው በሁለቱ የእሳት ክንፋቸው ፊታቸውን ይሸፍናሉ፡፡ ግሩም የሚሆን
ብርሃኑ (ነበልባሉ) እንዳይመታቸው በሁለት የብርሃን ክንፋቸው እግራቸውን ይሸፍናሉ፡፡ እረቂቅ በሚሆን ሁለት ክንፋቸው እስከዓለም
ዳርቻ ይወጣሉ፡፡
ሱራፌል በአለቆቻቸው፤ ኪሩቤልም በምስጋናቸው፤ መላእክትም በየሥርዓታቸው፤ ትጉሃንም በየሠራዊታቸው፤ የትጉሃንም አለቆች
በየወገናቸው፤ እሳትነት ያላቸው መላእክት በብርሃናቸው፤ መንፈሳውያን በአነዋወራቸው ግሩም በሚሆን ቃል ያመሰግናሉ፡፡
ይቀድሳሉ ከፍ ባለና በታላቅ ቃል ይጮሃሉ፤ ሲያመሰግኑም እንዲህ ይላሉ፤ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ
ፍጹም አሸናፊ እግዚአብሔር የጌትነትህ ምስጋና በሰማይና በምድር የመላ ነው፡፡
እኛም ከእነርሱ ጋር በአንድነት የጌታችንና የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አባት አንተ ቅዱስ ነህ፤
የጌትነትህም ምስጋና ግሩም ነው እንላለን፡፡ ይኸውም ብቻውን በእውነት ልጅህ ነው፤ አንተም ብቻህን በእውነት አባቱ ነህ፡፡
ከአንተ መወለዱ አይገኝም፤ ለአነዋወርህ ጥንት እንደሌለው ለእርሱም ለልጅህ ጥንት የለውም፣
ፍጻሜም የለውም፤ ለዘመንህም ጥንት እንደሌለው ለዘመኑ ጥንት የለውም፡፡
ከአንተ ከተወለደ ከልጅህ በቀር በቀኝህ የሚቀመጥ የለም፤ በዙፋንህም ላይ የሚቀመጥ የለም፤ እንደ አንተ ያለ አርዐያህና
አምሳልህ ነው እንጂ፡፡
ይኸውም ልጅህ የምክርህ አበጋዝ ነው፡፡ ከአንተ የተገኘ ወዳጅህ አምሳልህና መልክህ፤ ኅሊናህና
ኃይልህ፤ ጥበብህና ምክርህ፤ ቀኝህና ክንድህ፤ ከእውነተኛ ባሕርይህ የተወለደ እውነተኛ አምላክ ወልድ ዋሕድ ነው፡፡
በሁሉ ፍጹም የሚሆን ቃል ከባሕርይህ ወጣ፡፡ ከአንተ የተወለደ አርዐያህ ከአንተ ጋራ የሚተካከል ከአንተ ጋራ ልዑል
ግሩም የሚሆን ፡፡
መላእክትና የመላእክት አለቆች ይሰግዱለታል፤ ሰውን በመውደድህ ወደእኛ ሰደድኸው ወደኸናልና፡፡
እርሱ ራሱን አዋርዶ አዳነን ፤ ከአንተ የተወለደ እንደአንተ የሆነው በእኛ አምሳል ከእኛ ተወለደ፤ ይኸውም የሚመስልህ
ነው፡፡
ይህ በእኛ አምሳል በመካከላችን ተመላለሰ፡፡ ፍጹምነቱ ከአንተ ጋራ የሚተካከል የሚመስልህና እንደአንተ ያለ እርሱ ነው፡፡
የአነዋወርህን ነገር እርሱ ነገረን እንደ እኛ ሥጋ ሆነ፡፡ ዳግመኛም በአርያም ሱራፌልን የሚያስደነግጣቸው እርሱ በፈቃዱ ታመመ፡፡
ዐይተን አቃለልነው፡፡ በአንተ ዘንድ ገናና እንደመሆኑ መጠን በእኛ ዘንድ ጌታ የተመሰገነ ነው፤
ከትጉሃንም የተሠወረ ነው፤ በእኛ ባሕርይ ተወልዶ በእውነት ተገልጦ ታየ፡፡
በመልክ በብርሃን አንተን ይመስላል፤ ሰው ሆኖ ሥጋችንን መሰለ በእኛም አምሳል ከእኛ ዘንድ ኖረ፤ እንደአንተም የተመሰገነ ነው፡፡
ወጣ፣ ወደ አኛም ወረደ እንደ እኛ ተሰደበ ፡፡ ወጣ ወደ አንተም ዐረገ እንደአንተም የከበረ
ነው ፡፡
ትጉሃን በሰማያት የሚያመሰግኑት እርሱ የእሾህ ዘውድ ደፋ፤ ከወንበዴዎችም ጋራ በዕፀ መስቀል ላይ ተሰቀለ፤ ልዑላኑ
እየፈሩ በፊቱ እራሳቸውን የሚያዋርዱለት እርሱ በሚሰቅሉት ፊት ለሕማም እራሱን አዋረደ፡፡
ሰማይንና ምድርን የተሸከመውን በዕፀ መስቀል ላይ ደካማ እንጨት ተሸክመው፤ ሰማይና ምድር የሚንቀጠቀጡለትን
ጠባብ መቃብር በተቀበረበት ጊዜ ወሰነው፡፡
የዓለምን ዳርቻ በመኻል እጁ የሰበሰበውን፤ የዓለምንም ባሕር በእፍኙ የዘገነውን በበፍታ ገንዘው በሦስት ክንድ ከስንዝር
መቃበር ቀበሩት፡፡ ክቡር ራሱን ዘረጋ፤ ከእርሱም የተነሣ መቃብር ተመላ ፡፡
በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ወዳሉበት ደጅ ተዘግቶ ሳለ ገባ፡፡
ከደቀ መዛሙርቱም ተለይቶ ወጣ፡፡
በዚያም ሳለ ጌትነቱ ሰማያትን መላ፡፡ ወደ ሰማይም ዐረገ፤ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ ሰማይ ዙፋኑ ሆነ ምድርም የእግሩ
መመላለሻ፡፡
ዳግመኛም ሕያዋንንና ሙታንን ይገዛ ዘንድ ይመጣል፡፡ ከላይ ነጐድጓዱ ይሰማል፤ ቃሉም የምድርን
መሠረት ያናውጣል፡፡ ሙታንም ከመቃብራቸው ወደ እርሱ ይወጣሉ፡፡ ከአባቱ፣ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ክብር ምስጋና ለዘለዓለሙ የርሱ
የሚሆን ፡፡
አቤቱ በእውነት በቃልህ፤ ሁሉን በሞትህ ያስነሣሃቸው፤ ሙታንንም የምታስነሣ አንተ ነህ፡፡ ከከሃድያንም ወገን በመስቀልህ
ያመኑብህ፤ ከስሑታንም ወገን በሞትህ የተመለሱ፣ በኃጢአት ከተዳደፉት ወገን በመከራህ የተቀደሱ፤ ከሙታንም ወገን በትንሣኤህ ያስነሳሃቸው፤
በአንተ ለመፍረድ ከተሰበሰቡ ወገን ያመኑብህ፡፡
የብረትን መዝጊያ ከፍተህ ሥጋቸው በመቃብር የጠፋውን ታስነሣቸዋለህ፡፡ በሕይወታቸው ያንቀላፉትን
ታነቃቸዋለህ፤ በመሬት የተኙትንም ታስነሣቸዋለህ፡፡ ኃጥአን ባሮችን ነፃ ታደርጋቸዋለህ፡፡ የተዳደፉትን በምህረትህ ታከብራቸዋለህ፡፡
በይቅርታህ ዐላውያንን አንድ ታደርጋቸዋለህ (ታስማማቸዋለህ)፤ የተመለሱትን በቃልህ ታጸናቸዋለህ፡፡ በጎዳናህ ይሄዱ
ዘንድ አላውያንን ትመልሳቸዋለህ፤ ወደቦታህ ይገቡ ዘንድ የተበተኑትን ትሰበስባቸዋለህ፡፡
ከወገኖችህ የበደሉትን አንተን ወደ ማመን ትመልሳቸዋለህ፡፡
የመንፈስ ደካሞችን አቤቱ አንተ ታጸናቸዋለህ፡፡ በምድር የሚኖሩ ሁሉ አንተ አምላክ እንደሆንህ ያውቁህ ዘንድ፤ ከአንተ
የተወለደው የምትወደው ልጅህና ወዳጅህ የላክኸው ኢየሱስ ክርስቶስንም፤ ከእርሱ ጋራ ክብር ያለህ፤ ሥውር ከሚሆን መንፈስ ቅዱስም
ጋራ ለዘለዓለሙ፡፡