‘‘ እማይዬ እናቴ እኔ በበኩሌ ይህን ለሚያክል ትልቅ ሐሳብሽ ዲግሪ ይገባሻል ብያለሁ፡፡’’
‘‘ድግሪው ቀርቶብኝ እግዚብሔር ጸሎቴን ከሰማልኝ ይበቃኛል፡፡’’
‘‘የትኛውን ጸሎትሽን?’’
‘‘ሁለቱን ጸሎቶቼን ከሰማኝ ስለሌላስ አለምነውም ነበር፡፡’’
‘‘ሁለቶቹ ጸሎቶችሽ ምን የሚሉ ናቸው፡፡’’
‘‘አንደኛው አቤልዬ በግቢ ጉባኤ የጀመረውን ግብረ ዲቁና አስጨርሶት ዲያቆን ሆኖ እንዲያሳየኝ፣ ሁለተኛው ደግሞ አልዓዛርዬ
ሰንበት ትምህርት ቤት ገብተህ ስትማርና ስታገለግል እንዲያሳየኝ፡፡ ’’
‘‘ይህን ያህል እናቴ! ይህ ነገር ላንቺ ይህን ያህል ትልቅ ነገር ነው?’’ ታላቄ ልቡ ስብር ብሎ ነበር የጠየቃት፡፡
‘‘እንዴታ አልዓዛርዬ! እንዴታ! እኔ እኮ እናንተን በእነዚህ ሁሉ አመታት ውስጥ ብቻዬን ሳሳድጋችሁ ከእግዚአብሔር
በቀር የረዳኝ ማንም አልነበረም፡፡ የምትፈልጉትን ሳላደርግላችሁ እንዳልቀር እየሰጋሁና እየተሳቀቅሁ ስኖር በበረከቱ የጎበኘኝ፣ የማጣቴን
ወራት ያሳለፈልኝ፣ ብቸኝነቴን ያስረሳኝ እግዚአብሔር እኮ ነው፡፡ ዛሬ ስላደጋችሁ እኮ ነው ቁጭ ብላችሁ የምታጫውቱኝና አብራችሁኝ
የምታመሹት፤ ትናንት ግን እናንተን ገና በጊዜ አስተኝቼ ረጅሙን የጸጥታ ሌሊት በብቸኝነት ሳነጋ አብሮኝ የሚያነጋው የቅርቤ ሰው
የምለው ከእግዚአብሔር በቀር ማንም አልነበረልኝም፡፡ ታማችሁ ስታተኩሱብኝ በምን ገንዘብ አሳክማችኋለሁ ብዬ ስጨነቅ የነፃ ሐኪሜና
መድኃኒቴ ከአምላኬ ሌላ ማንም አልነበረልኝም፡፡ ታዲያ እንዲህ ላለው ባለውለታ ምኑን ይከፍሉታል? ምንስ ይሰጡታል? ብዙ አመት አውጥቼና
አውርጄ የደረስኩበት ድምዳሜ ለእግዚአብሔር የምሰጠው አምሀዬ የእናንተ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ የአገልግሎት ሕይወት ነው፤ እንጂማ
ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ሌላ ምን ነገር ሊኖረን ይችላል?’’
ታላቅ ወንድሜ ራሱን መቆጣጠር አልቻለም፤ ለደቂቃዎች ስቅቅ ብሎ አለቀሰ፡፡
‘‘ተይ እባክሽን እማዬ፣ ተይ ከኅሊናዬ በላይ አትሁኚብኝ’’ ከተቀመጠበት ተነስቶ አንገቷ ስር ተሸጎጠ፡፡ እማዬም
ጸጉሩን በፍቅርና በስስት መዳበሷን ቀጠለች፡፡
‘‘ አታስቢብኝ እናቴ፣ ሐሳብ አይግባሽ የእኔ እናት፡፡ በአንቺ ውስጥ ስላሳየኝ ፍቅሩ ስል እግዚአብሔርን አብዝቼ
እወደዋለሁ፣ በአንቺ ውስጥ አድሮ ያሳየኝን ፍለጋውን እከተላለሁ፣ በእናቴ ቃል ውስጥ ለተናገረኝ ትምህርቱ እታዘዛለሁ፡፡’’ አልዓዛር
አሁንም ማልቀሱን አላቆመም ነበር፤ እማዬም በጸጥታ እያነባች ነበር፡፡ የእናቴን እንባ ሳይ ውስጤ ተንሰፈሰፈብኝ፤ እማይዬ የእኔ
የዋህ፣ የእኔ የፍቅር ሰው፣ የእኔ ይቅር ባይ፣ የእኔ ተለማማጭ፣ የእኔ … እኔ ራሴ እንባዬን መቆጣጠር ተሳነኝ፡፡ ተነስቼ ተጠመጠምኩባቸው፡፡
በእውነተኛው ፍቅሯ ሁለታችንንም ጭምቅ አድርጋ አቀፈችን፡፡ የሆነ ደስ የሚል መታቀፍ፣ ቃላት ሊገልጹት በማይችሉት መጠንና ልክ የሆነ
የፍቅር እቅፍ፣ ከእቅፏ ባልወጣ ስል ተመኘሁ፡፡ ማስመሰል የሌለበት፣ ከበጎነትና ከእናትነት የሚመነጭ ማቀፍ … ደስ በሚለው በእናቴ
እቅፍ ውስጥ ሆኜ ክርስቶስን አሰብኩት፡፡ የእናቴ ፍቅር እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ የወደደበትን፣
ወልድን እስከሞት ያደረሰውን ፍቅር ሰበከኝ፡፡ ከንፈሮቼ ቃል ባያወጡም ልቤ ግን አሰምቶ ተናገረ፡- እማይዬ ዲያቆን ሆኜ ታዪኛለሽ
እሺ! እናትዬ ልነግርሽ ስለማልፈልግ እንጂ አይደለም ዲያቆን ልሆንለት፣ አይደለም በሕይወቴና በኑሮዬ፣ ቢሆንልኝስ በሞቴ እንኳን
ቢሆን ጌታዬን ብመስለው፣ ባከብረው እወዳለሁ፡፡
ብዙ ደቂቃዎች ጸጥ ብለው በፍጥነት አለፉ፡፡ ሁላችንም ግን ውስጣችንን በተመስጦ እያዳመጥን ነበር፡፡ ግማሽ ሰዓት
ያህል ካለፈ በኋላ
‘‘እማዬ አንዳይደክምሽ ግቢና ተኚ ’’ የሚለው የስምረት ድምጽ ሁላችንንም ከየሔድንበት የማይታይ ሐሳባዊ ዓለም መለሰን፡፡
እናታችን ሁለታችንንም ግንባራችንን ስማን ተነሳች፡፡
‘‘አቤል ’’
‘‘አቤት አልኣዛር’’
‘‘አሁን ምንድን ነው ማድረግ ያለብን?’’
‘‘በመጀመሪያ በኑሯችን እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት፣ በዚህ ወስጥ ደግሞ እማዬ የምትፈልገውን ኑሮ መኖር፡፡ እኔ እናቴን
ደስ ማሰኘት እፈልጋለሁ፡፡ እናቴን ደስ ማሰኘት ስችል ብቻ አምላኬንም ደስ ማሰኘት እንደምችል ገብቶኛል፡፡ በቅርቤ ያለችውን እማዬን
ደስ ሳላሰኝ እግዚአብሔርን ፍለጋ በሩቅ መንገድ ራሴን አላደክምም፡፡ እግዚአብሔር እናቴ ውስጥ ነው ያለው፤ ስለዚህ እርሱን ፍለጋ
ሩቅ መሔድ አያስፈልገኝም፡፡’’
‘‘ልክ ነህ አቤልዬ! በእናታችን ውስጥ የተናገረን እግዚአብሔር ነው፡፡ እኔም ከእንግዲህ በሰንበት ትምህርት ቤት
አገልግሎት ውስጥ ድርሻ ይኖረኛል፡፡ እማዬ ከእኛ በተሻለ ስለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ስለ ሰንበት ትምህርት ቤቶች መጠናከር
ይህን ያህል መረዳት ካላት እኛ ወጣቶቹማ ከዚህ የበለጠ ድርሻ ሊኖረን ይገባል፡፡ እርሷ እንዳለችው የሰንበት ትምህርት ቤት አገልግሎትን
እኛ መደገፍ ካልቻልን ማን ሊደግፍ ይችላል? ዛሬ ወጣቶች ላይ መስራት ያልቻለች ቤተ ክርስቲያን ነገ የምትለው ነገር ሊኖራት ስለማይችል
ሰንበት ትምህርት ቤቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችን ነገዎች ናቸው፡፡ ለዚህ ነገር ደግሞ እኔም የራሴ ድርሻና ኃላፊነት ሊኖረኝ እንደሚገባ
አምኛለሁ፡፡ እማዬ ደስ እንዲላት ብቻ ሳይሆን ሐሳቧ ትክክል ስለሆነና ስላሳመነኝም ጭምር ከነገ ጀምሬ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋይ
እሆናለሁ፡፡ አቤልዬ አንተም ታዲያ በግቢ ጉባዔ አገልግሎትህ መጠንከርና ግብረ ዲቁናውንም በደንብ መከታተል አለብህ፡፡ ዛሬ ግቢ
ጉባዔ ላይ በደንብ መስራት ከቻልን ነገ ከግቢ ስትወጡ የምትመጡት ወደሰንበት ትምህርት ቤት ነው፡፡ ሌሎች ሊያደርጉት ስለሚገባቸው
ጉዳይ ሳይሆን እኛ ልናደርገው ስለምንችለውና ልንፈጽመው ስለምንችለውም ነገር ብቻ ማሰብ እንጀምር፡፡’’
‘‘ትክክል ነው፡፡ አንድ ሰው ብዙ መሆኑንና ብቻውን ሆኖ ብዙዎችን መለወጥ እንደሚችል ከእናቴ ተምሬአለሁ፡፡ እማዬ
ብቻዋን በእኔ፣ በአንተና በስምረት ላይ በጎ ተጽዕኖ መፍጠር ችላለች፡፡ እኛም ለለውጥ ከተንቀሳቀስን እንዲሁ በጎ ተጽዕኖ የምናሳድርባቸው
ሌሎች ሰዎች ይኖራሉ ማለት ነው፡፡ እንዲህ ማድረግ ስንችል ብቻ ጌታችን እንዳዘዘን ዓለሙን የምናጣፍጥ የምድር ጨው መሆን እንችላለን፡፡’’
‘‘እውነት ነው የተጠራነውም ለዚህ ነው፡፡ ክርስቶስ የተወልን የመንገዱ ፍለጋ ሌሎችን ማገልገል ነው፡፡ እኔ እንደወደድኳችሁ
እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትዕዛዜ ይህቺ ናት ያለን ለሌሎች ሰዎች የሚተርፍ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲኖረን ነው፡፡ ክርስትና
እኮ ሌሎችን ማገልገል ነው፡፡ ስለሌሎች ግድ የሌለው ክርስቲያናዊ ሕይወት ሊኖር አይችልምና፡፡’’
‘‘ይህ ለእኔ የእግዚአብሔር ጥሪ ነው፡፡ ይህንን ጥሪውን ደግሞ ቸል አልልም፡፡ እኔ በግቢ ጉባኤ አንተም በሰንበት
ትምህርት ቤት አገልግሎት እንበርታ፡፡ ያን ጊዜ እግዚአብሔርን፣ ቤተ ክርስቲያናችንን፤ እናታችንንና ራሳችንን ደስ ማሰኘት እንችላለን፡፡’’
‘‘አይ አቤል እኳንም ግን ታናሼ ሆንክ! ’’
‘‘እንዴ ለምን? ታላቅህ ሆኜ ቢሆን ኖሮስ?’’
‘‘ታላቄ ብትሆን ኖሮማ እነዚህ ምርጥ ሐሳቦችህ ይህን ያህል አያስደንቁኝም ነበር፡፡’’
‘‘መቼም እኔን እንደማሞካሸት የምትወደው ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡’’
‘‘ለማሞካሸት ሳይሆን የምሬን ነው፡፡ ለማንኛውም በጣም ስላመሸን የንዋም ጸሎታችንን እናድርስና እንተኛ፡፡’’
‘‘እሺ’’ ሁለታችንም ለጸሎት ተነሳን፡፡
ስለሁሉም የአባቶቻቸንን አምላክ በጸሎት አመስግነንና ስለነገም ለምነነው ወደ መኝታችን ልንሔድ ተነሳን፡፡
‘‘በል በሰላም እደር፡፡’’ መኝታ ክፍሌ ድረስ ሸኝቶኝ
ተሰነባበትን፡፡ ወደ መኝታ ክፍሌ እየገባሁ ሳለ፡-
‘‘አቤል’’ ሲል ጠራኝ
‘‘አቤት አልዓዛር ’’ ቶሎ ወደ ወንድሜ ዘወር አልኩኝ፡፡
ግን ምንም አላለኝም፡፡ ሁሌ እንደሚያደርገው ዝም ብሎ እያየኝ ነበር፡፡ ይህ አስተያየት የታላቅ ወንድሜ ብቻ ነው፡፡
ማንም ሰው እንደዚህ አያየኝም፡፡ ዝም ባለ እይታው ውስጥ ለእኔ ያለውን ፍቅርና አክብሮት፣ በእኔ ላይ ያለውን እምነትና ተስፋ፣
የታላቅነት ጥንቃቄውንና እንክብካቤውን … እመለከታለሁ፡፡ እኔስ ብሆን ከዚህ ፍቅርና ክብር ወዴት ፈቀቅ እላለሁ! በዝምታችን ውስጥ
ለደቂቃዎች ያህል አወራንና ዝም እንደተባባልን ወደየመኝታችን አመራን፡፡ ሁልጊዜም እንደዚህ ነው፡፡ ከታላቄ ጋር አንድም ቀን ተሰለቻችተን
አናውቅም፡፡ በዚህ ሁሉ አመታት ውስጥ የወንድሜን ፍቅር አልለመድኩትም፣ በየቀኑ ለእኔ አዲስና እንግዳ ነገር ነው፡፡ … የታላቄን ፍቅርና እንክብካቤ እያሰብኩ መኝታ ክፍሌን ቆለፍኩና ብቻዬን ከአምላኬ
ጋር ላወራ በፊቱ ተንበረከክሁ፡፡
በሰዎች ፍቅር የከበበኝን፣ በቤተሰባችን ውስጥ ፍቅርንና መተሳሰብን ያበዛልንን አምላካችንን አመሰገንኩት፡፡ በጣም
የምገረምበትንና ውስጤ የሚነካበትን የእናቴንና የወንድሜን ፍቅር ሳስብ የጌታዬን ፍቅር ያስታውሰኛል፡፡ ፈራጅነት የሌለበት፣ ቅን፣
መቼም ቢሆን ማንንም የሚቀበልና መጸየፍን የማያውቅ ፍቅሩ፣ ለሞት አስከሚደርስ ድረስ እኔን የፈለገበት እውነተኛ መውደዱ፣ ነውሬን
ያራቀበት በሰው ሁሉ ፊት እርቃኑን የተሰቀለበት ትዕግስቱ … ይህን ሁሉ አስባለሁ፣ በእናቴና በወንድሜ ፍቅር ውስጥ የክርስቶስን
ፍቅር አስታውሳለሁ፣ እርሱንም ብቻ እናፍቃለሁ …