ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ሁለቱ፤ከሰብዓ ሁለቱ አርድእትም ሁለቱ በመንፈስ ቅዱስ ተመርጠው ቅዱስ ወንጌልን በመጻፋቸው አራቱ ወንጌላውያን ተብለው ይጠራሉ፡፡ እነሱም ቅዱስ ማቴዎስ፣ ቅዱስ ማርቆስ፣ ቅዱስ ሉቃስ እና ቅዱስ ዮሐንስ ናቸው፡፡ የተከበራችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ዛሬ በዚህ አምድ ከሰብዓ ሁለቱ አርድእት መካከል አንዱ ስለሆነው ስለቅዱስ ማርቆስ እና ስለጻፈው መጽሐፍ (ወንጌል) እናያለን፡፡
በመጀመሪያ ቅዱስ ማርቆስ ማን ነው?
ቅዱስ ማርቆስ ሐዋርያና ወንጌላዊ እንዲሁም ሰማዕት ነው፡፡ በተጨማሪም የእስክንድርያ (ግብጽ) ቤተ ክርስቲያን መስራች አባትም ነው፡፡ እናቱ ማርያም ስትባል አባቱ ደግሞ አርስጦሎስ ይባላል፡፡ የመጀመሪያ ስሙም ዮሐንስ ይባል ነበር፡፡ በትውልዱ ዕብራዊ ሲሆን ቤተሰቦቹ ግን ይኖሩ የነበሩት ሲረኒካ በተባለችውና በዛሬዋ ሊቢያ ምዕራባዊ ጠረፍ በተቆረቆረችው ከተማ ነበር። ነገር ግን የሰሜን አፍሪቃ ዘላን ጎሳዎች በየጊዜው በከተማው ጥቃት እየሰነዘሩ ቤተሰቦቹን አላስቀምጥ ስላሏቸው ወደ ትውልድ ሀገራችው ኢየሩሳሌም በመመለስ ቤት ሰርተው ተቀመጡ። ቅዱስ ማርቆስ ገና በልጅነቱ ኢየሩሳሌም ለመኖር በመታደሉ በዚያን ጊዜ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ አውራጃዎች እየተዘዋወረ የሚያስተምረውን ትምህርት የማግኘት ዕድል ነበረው። የላቲን፣ የግሪክና የዕብራይስጥ ቋንቋዎችን አሣምሮ ያውቅ ነበር። የማርቆስ እናት ቤቷን ለክርስቲያኖች መሰብሰቢያነት የሰጠች ደገኛ ሴት ነበረች። ሁል ጊዜ ቅዱሳን ሐዋርያት በእናቱ ቤት እየተሰበሰቡ ጸሎት ያደርጉ ነበር። በቤቱም ሁለት ድንቅ ተዓምራት ተደርገዋል እነሱም ጌታ የመጀመሪያውን የሐዲስ ኪዳን ቁርባን ለሐዋርያት አቁርቧቸዋል። እንዲሁም በበዓለ ሀምሳም መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደላቸው በርስዋ ቤት ተሰባስበው ሲፀልዩ ነው።
ቅዱስ ማርቆስም በቤቱ የጌታን ትምህርት ሰምቶ ልቡ ስለተነካ ሁሉንም ነገር ትቶ የክርስቶስን ወንጌለ መንግሥተ ሰማያት ለመስበክ ቆርጦ ተነሳ፡፡ በተጨማሪም የአባቱን እህት ቅዱስ ጴጥሮስ ስላገባት ከእርሱ ጋር በቀላሉ ለመተዋወቅ ችሏል። ጌታ ካረገ በኋላ ሐዋርያት ዓለምን በዕጣ ተከፋፍለው ሲወጡ ከሐዋርያው ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር በመጀመሪያው ጉዞ በ46 ዓ.ም ለስብከተ ወንጌል ወጥቶ ነበር። ነገር ግን እናቴ ናፈቀችኝ ብሎ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ። ከዚያም ከሐዋርያው ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር መኖር ጀመረ። ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር በመሆን በታናሿ እስያ አድርገው እስከ ሮም ድረስ ወንጌልን አስተምረዋል። በመጨረሻም በ60 ዓ.ም ወደ ሰሜን አፍሪቃ በመምጣት በዘመኑ ታዋቂ የንግድ፣ የባህልና የፖለቲካ ማዕከል ወደ ነበረችው እስክንድርያ ደረሰ። በጊዜውም የእስክንድርያ ሰዎች ጣዖት አምላኪዎች ስለሆኑ በዚያ ብዙ ፈተና ደረሰበት። ከብዙ ድካም በኋላ የመጀመሪያዋን ቤተ ክርስቲያን አንያኖስ በተባለ ጫማ ሰፊ ቤት በግብፅ መሰረተ። ከዚያም ስለ ክርስቶስ ብዙ በመስበክ ተጨማሪ አብያተ ክርስቲያናት ወደ ትውልድ ሀገሩ ሲረናይካ ጭምር በመሄድ አንፆአል። በ68 ዓ.ም የትንሣኤ በዓልን በግብፅ ቅድስት ባውክልያ በተባለ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከእስክንድርያ ክርስቲያኖች ጋር በሚያከብርበት ዕለት የግብፅ ጣዖት አምላኪዎች ተነሱበት። በዚያ ዓመት የትንሳኤ ዕለት ከታወቀው የግብፃውያን ጣዖት ሰራፒየም በዓል ጋር ስለገጠመ ቤተክርስቲያኑን ሰብረው በመግባት ቅዱስ ማርቆስን ያዙት። ከሠረገላ ጋር በማሰር ቀኑን ሙሉ ሲጎትቱት ዋሉ። በመጨረሻም ሚያዚያ 30 ቀን ዐረፈ። ሥጋውንም ለማቃጠል እንጨት ሲሰበስቡ ሐይለኛ ዝናብ በመጣሉ ተበታተኑ ከዚያም የእስክንድርያ ምእመናን ሥጋውን ደብቀው በቅድስት ባውክልያ ቤተክርስቲያን አሳረፉት።
ምልክቱ
ቅዱስ ማርቆስ በአንበሳ ተመስሏል፡፡ ምክንያቱም አንበሳ በቅዱስ መጽሐፍ ለእግዚአብሔርም ለሰውም ምልክት እንደሆነ ብዙ ጊዜ ተጠቅሶአል (ትን. ሆሴዕ፤13፡7 1ኛ.ነገ፤ 10፡ 19-20)፡፡ በአንበሳ የተመሰለበት ዐቢይ ምክንያት ግን በግብጽ የነበሩትን የአንበሳ ጣዖታት በስብከቱ አጥፍቶ አንበሳ ዕጉለ አንበሳ የተባለውን ክርስቶስ በመስበኩ ነው፡፡
የጻፈው ወንጌል
በመጀመሪያ ቅዱስ ማርቆስ ከሐዋርያው ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር በመሆን በሮም ያስተምር ነበር፡፡ ከዚያ ግን ቅዱስ ጴጥሮስ በዚያው ሮም ሲያስተምር ቅዱስ ማርቆስ ግን አብዛኛውን ትምህርት ያስተማረው በግብጽ ነው፡፡ በመቀጠልም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ከጌታ የሰማውን እና የተማረውን ጌታ ባረገ በአሥራ ሁለተኛው ዘመን ወንጌሉን ጻፈው፡፡ ወንጌሉም 16 ምዕራፎችእና 661 ቁጥሮች ሲኖሩት ከአራቱ ወንጌላውያን የመጀመሪያው መጽሐፍ ነው፡፡ እንዲሁም አጭሩ ወንጌል ነው። ከትረካ ይልቅ ድርጊቶችን በቅደም ተከተል ያስቀምጣቸዋል። ወንጌሉን የጻፈው ለአረማውያን ያውም ለሮማውያን በመሆኑ ከሌሎች ወንጌላውያን የተለየ አገላለጥና አጻጻፍ ተጠቅሟል። የተፃፈበት ቋንቋ ሮማይስጥ ነው። የወንጌሉ ዋና መልዕክት የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት፣ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅነት መግለጥ ነውና ሲጀምርም ሲጨርስም ገልፆታል። በአብዛኛውም ሮማውያን ትልቅ ነን ብለው ስለሚያስቡ የወንጌሉ አጻጻፍ ከእነርሱ በላይ ኃያል ንጉስ እንዳለ ለመግለጥ ነው። ይህም ጌታ በአጋንንት ላይ ያለውን ስልጣን፣ በሽተኞችን ስለመፈወሱ፣ የአለም ጌታ ስለመሆኑና ፈጣሪ መሆኑን በደንብ ያስረዳል። ለምሳሌ፦ በሽተኞችን ፈወሰ (1፥ 34)፣ በባሕር በመርከብ ሄደ ተአምራት አደረገ (4፥41፣6፥48፣54) ወ.ዘ.ተ እያለ የጠቀሰ ሲሆን ስለ መከራ (መስቀል) እና ደቀመዝሙርነትም በሰፊው ገልጧል፡፡
እሲኪ ደግሞ እያዳንዱን ምዕራፍ በአሰሳ ንባብ እንየው:-
የመጀመሪያው ምዕራፍ የሚነግረን ስለመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ጥምቀት፣ ስለ ዮሐንስ የኑሮ ሁኔታ እና መመረጥ፣ ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትሕትና ይኸውም በዮሐንስ እጅ ስለመጠመቁ ነው፡፡ በዚያም ምሥጢረ- ሥላሴ መገለጡን ይነግረናል፡፡ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት በምድረ በዳ መሰንበቱንና መጾሙን፣ በመቀጠልም ሐዋርያትን ከተለያዩ ቦታ መምረጡንና ከዚያም ብዙ በሽተኞችን ስለማደኑ ይነግረናል፡፡
ምዕራፍ 2፡ ስለመጻጉዕ መዳን፤ ከኃጢያተኞችና ከቀራጮች ጋር በመብላቱ ጻፎችና ፈሪሳውያን ቢጠይቁት እኔ ኃጥኣንን እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም እንዳላቸው፣ ወደፊት ሐዋርያቱ የሚጾሙበት ቀን እንደሚመጣ እንደነገራቸው፤ በተጨማሪም ስለሰንበት በጠየቁት ጊዜ ሰንበት ስለሰው ተፈጠረች እንጂ ሰው ስለሰንበት አልተፈጠረም ማለቱን ይነግረናል፡፡
ምዕራፍ 3፡ ጌታችንና አምላከችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሌሎች ብዙ ተአምራት ማድረጉን፤ ሐዋርያትን ስለመምረጡ እነሱም፡ ስምዖን (በኋላም ጴጥሮስ)፣ የዘብዴዎስ ልጅ ያዕቆብ፣ ዮሐንስ፣ እንድርያስ፣ ፊልጶስ፣ በርተሎሚዎስ፣ ማቴዎስ፣ ቶማስ፣ የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብ፣ ታዴዎስ፣ ቀነናዊው ስምዖን እና ያስቆሮቱ ይሁዳ መሆናቸውን፤ በተጨማሪም የኔን ፈቃድ የሚያደርግ ሁሉ እርሱ የኔ ነው ማለቱን ይነግረናል።
ምዕራፍ 4፡ የሚነግረን ስለዘሩ ምሳሌ ነው፡፡ ይህም ሰው ዘርን ዘርቶ ለማጨድ የሚዘራበት ቦታ እንደሚወስነው ነው። የእግዚአብሔር መንግስትም መልካም ዘርን በምድሩ ላይ እንደሚዘራ ሰው እንደዚሁ ናት ብሎ ጌታችን እንዳስተማራቸው ይነግረናል። በተጨማሪም የእግዚአብሔርን መንግስት በስናፍጭ ቅንጣት መስሏታል።
ምዕራፍ 5፡ ጌታችን ብዙ በሽተኞችን እንደፈወሰ፤ በአጋንንት ላይ ስላለው ስልጣን በሰፊው ይነግረናል። ለምሳሌ፡ ኢያኢሮስ የተባለውን የምኩራብ ሹም ልጅ ከሞት አስነስቷታል።
ምዕራፍ 6፡ ደግሞ ጌታችን በናዝሬት ስለማስተማሩና ሐዋርያትን ያስተምሩ ዘንድ ወደ ተለያየ ቦታ መላኩን ይነግረናል። ስለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ይህም ሄሮድያዳ በተባለች ሴት አዛዥነት በሄሮድስ ጭፍሮች አማካኝነት አንገቱ ተቆርጦ ሰማዕትነት እንደተቀበለ ይተርክልናል። ከዚያም ሐዋርያት ወደ ጌታ እንደተመለሱ ህዝቡም ወደ እነሱ እንደተሰበሰበ ቦታውም ምድረ በዳ ስለነበርና የሚበሉትም ስለሌላቸው ጌታችን ሁለቱን ዓሣዎችንና አምስቱን እንጀራ እንደባረከላቸውና አበርክቶ እንደመገባቸው ያስረዳናል። በተጨማሪም ጌታችን በጌንሴሬጥ ብዙ ተአምራት ስለማድረጉ ያወራል።
ምዕራፍ 7፡ በዋናነት ጌታ ስላደረጋቸው ብዙ ተዓምራት እነሱም ዲዳውንና ሌሎችንም ስለመፈወሱ፣ ከሲሮፊኒቃዊት ሴት ልጅ ጋኔን ማውጣቱን እንዲሁም ጌታችን ፈሪሳውያንን ስለመገሠጹ ይነግረናል።
በምዕራፍ 8፡
ምልክት ስለሚሹ ሰዎች ሲናገር ይህ ትውልድ ስለምን ከሰማይ ምልክትን ይሻል እንዳለ፣ በቤተ ሳይዳ አይነ ስውር ስለማዳኑ፤ አራት ሺህ ያህል ሰዎችን በምደረ በዳ አምስቱን ዓሳና ሰባት እንጀራ ባርኮ እንዳበላቸው፣ ኢየሱስም ደቀመዛሙርቱን ሰዎች እኔን ማን ይሉኛል ብሎ እንደ ጠየቃቸው ይነግረናል። በተጨማሪም የሰው ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስ) ብዙ መከራ ሊቀበል፣ ሊገደልም ከሦስት ቀንም በኋላ ሊነሣ እንዳለው ያስተምራቸው እንደጀመር፤ በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ ብሎ እንዳስተማራቸውም እናነባለን።
ምዕራፍ 9፡ ጌታችን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ወደ ደብረታቦር ተራራ ወጥቶ ክብሩን መግለፁን ይነግረናል። ሌሎች ተአምራት ማድረጉንም ያስረዳናል፤ እንዲሁም ጌታችን ስለሚደርስበት መከራ እና ሞት፤ ትህትናን ስለማስተማሩ፣ ስለፍቅርም ይናገራል፡፡
በ10ኛው ምዕራፍ ስለ ጋብቻ ስለተሰጠው ትዕዛዝ ይህም ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል ሁለቱም አንድ አካል ይሆናሉ ብሎ ፈሪሳውያንን እንደአስተማራቸው፣ ሕጻናትንም እንደባረካቸው፣ እንዲሁም ስለእርሱ ሁሉን ትተው የሚከተሉትን ዋጋቸው በሰማይ እንደሆነ፣ ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት የዘብዴዎስ ልጆች ዮሐንስና ያዕቆብ ስለጠየቁት ጥያቄም ይነግረናል።
ምዕራፍ 11 ደግሞ በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ስለመግባቱ ብዙ ሰዎችም ልብሳቸውንና የዘንባባ ዝንጣፊ በመንገድ ላይ እያነጠፉ ሆሣዕና በአርያም በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እያሉ ስለማመስገናቸው፣ ስለተረገመችው በለስና ቤተ መቅደስን ስለሚያረክሱ ሰዎች ይነግረናል። ከዚህም በመቀጠል በደልን ይቅር ስለማለት ሲያስተምር በሰማያት ያለው አባታችሁ ኃጢያታችሁን ይቅር እንዲላችሁ በማንም ላይ አንዳች ቢኖርባችሁ ይቅር በሉት ብሎ እንዳስተማረ፣ ጌታም ደግሞ በሁሉ ላይ ስልጣን እንዳለው ይተርካል፡፡
በምዕራፍ 12ም ስለ ወይን ዛፍ ምሳሌ፤ ፈሪሳውያን ስለግብር በጠየቁት ሰዓት ጌታችንም መልሶ የቄሳርን ለቄሳር የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ብሎ እንደመለሰላቸው፣ ትንሣኤ ሙታን የለም ከሚሉ ሰዱቃውያን ስለተነሳበት ጥያቄ፤ ከአንድ ጸሓፊ ስለቀረበለት ጥያቄ፤ ጌታችንም መልሶ ስለጠየቃቸው ጥያቄም ይነግረናል።
ምዕራፍ 13፡
ስለ ቤተመቅደስ መፍረስና ስለ ዓለም ፍጻሜ በደብ ረዘይት ተቀምጦ ሳለ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ዮሐንስና እንድርያስ ንገረን መቼ ይሆናል ብለው አንደጠየቁት፤ በመጨረሻ ሰዓትም የሰው ልጅ በብዙ ኃይልና ክብር በደመና እንደሚመጣ፣ ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም ብሎ ለደ ቀመዛሙርቱ እንደ ነገራቸው ይተርክልናል፡፡
በምዕራፍ 14 ውስጥ የካህናት አለቆችና ጻፎችም ጌታን እንዴት አድርገው ለመያዝ እንደተመካከሩ፤ አንዲት ሴት በጌታችን ራስ ላይ ሽቱ እንዳፈሰሰችበት፤ የአስቆረቱ ይሁዳ አሳልፎ ሊሰጠው ወደ ካህናት አለቃ መሄዱን፤ በጸሎተ ሐሙስም ጌታችን ከሐዋርያት ጋር የመጨረሻውን ራት አብሮ እንደበላ፤ ኢየሱስም ለሐዋርያት ዛሬ ሁላችሁም በእኔ ትሰናከላላችሁ እንደ አላቸው፤ ይሁዳም አሳልፎ እንደሰጠው ጴጥሮስም እንደካደው ይገልጻል።
ምዕራፍ 15 ደግሞ ኢየሱስን አስረው ለጲላጦስ አሳልፈው እንደሰጡት፤ ከዚያም በጌታ ላይ ብዙ መከራ እንደ አደረሱበት (ቀይ ልብስ እንዳለበሱት፣ የእሾህ አክሊል እንደደፉበት፣ እንደተዘባበቱበት፣ ሀሞት እንዳጠጡት፣ እንደሰቀሉትም፣ ልብሱንም ዕጣ እንደተጣጣሉበት)፣ በሰቀሉት ጊዜም ብዙ ተአምራት መደረጋቸውን ይነግረናል።
በመጨረሻው ምዕራፍ 16 ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ መነሳቱን፤ ለመጀመሪያ ጊዜ ያዩት መግደላዊት ማርያም፣ የያዕቆብም እናት ማርያም፣ ሰሎሜም መሆናቸውን፣ ከዚያም ጌታችን ሐዋርያት በማዕድ ተቀምጠው ሳለ ከይሁዳ ውጭ ለአሥራ አንዱ መገለጡን ይነግረናል። ከዚያም ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ግን ይፈረድበታል ብሎ ነገራቸው። በአጠቃላይ ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ የጌታን ስራ ሲገልጥ ከትሕትና ሥራው ጎን ሁል ጊዜ የኃይል ሥራውን አብሮ ያቀርባል።
ሙሉውን አንብባችሁ እንድትረዱት እየጋበዝን ለዛሬው እዚህ ላይ አበቃን በያለንበት እግዚአብሔር አምላክ ይጠብቀን፣ የእመ ብርሀን አማላጅነት የቅዱሳን ምልጃና ፀሎት አይለየን። አሜን።
No comments:
Post a Comment