Wednesday, November 9, 2016

ጸሎተ ቡራኬ




  •         ልዩ ሦስት የምትሆን አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሆይ የሚፋቀሩ የክርስቶስ ወገኖች የሚሆኑ ሕዝብህን በሰማያውያንና በምድራውያን በረከት ባርክ፡፡

  •        በእኛ ላይም የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ላክ፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንህንም ደጆች በምሕረትና በሃይማኖት እንዲከፈቱ አድርግልን፡፡ እስከ መጨረሻዪቱ  ሕቅታም ድረስ ልዩ ሦስትነትህን ማመንን ፈጽምልን፡፡
  •       ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የታመሙ ወገኖችህን ጎብኝ፤ የሄዱትንና እንግዶች የሆኑትን አባቶቻችንና ወንድሞቻችንን መርተህ በሰላምና በጤና ወደ ቤታቸው መልሳቸው፡፡
  •       የሰማዩን ነፋስ ባርክ፡፡
  •       ዝናሙንም፤ በዚህች ዓመት የሚያፈራውን የምድሩን ፍሬ እንደ ቸርነትህ ባርክ፡፡ ዘወትር ተድላንና ደስታን አድርግ፡፡
  •       ሰላምህንም አጽናልን፤ ሁልጊዜ ለኛ በጎ ነገርን ሊያደርጉልን ጽኑዓን የሚሆኑ የነገሥታቱን ልቡና መልስ፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያንህ ሁል ጊዜ ለሚሰበሰቡ ለቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ፍቅርን ስጥ፡፡ ለሁሉም ለእያንዳንዱ በየስማቸው ኃያላን በሚሆኑ በነገሥታቱ ፊት ሰላምን አብዛላቸው፡፡
  •          አምላካችን ሆይ በቀናች ሃይማኖት ሆነው ያንቀላፉትንና ያረፉትን የአባቶቻችንንና የወንድሞቻችንን፤ የእህቶቻችንንም ነፍስ አሳርፍ፡፡
  •          አምላካችን ክርስቶስ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ዋጋቸውን ይከፍላቸው ዘንድ ዕጣንና ቁርባን ወይንና ሜሮን ዘይትም መጋረጃም የንባብ መጻሕፍቶችን የቤተ መቅደስንም ንዋያት በመስጠት የሚያገለግሉትንም ባርክ፡፡
  •        ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ከእኛ ጋራ የተሰበሰቡትንም ሁሉ አምላካችን ክርስቶስ ሆይ ይቅር በላቸው፡፡ በሚያስፈራና በሚያስደነገጥ በመንበርህ ፊት ምጽዋት ያመጡትንም ሁሉ ተቀበላቸው፡፡
  •        የተጨነቀችዪቱን ነፍስ ሁሉ አሳርፍ፤ በሰንሰለት የታሠሩትን፤ በስደትና በምርኮ ያሉትንም፡፡ መሪር በሆነ አገዛዝ የተያዙትንም አምላካችን ሆይ በቸርነትህ አድናቸው፡፡
  •          መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ወደአንተ በምንማልድበት ጊዜ እንድናስባቸው ያዘዙንን ሁሉ በሰማያዊት መንግሥትህ አስባቸው፡፡ ኃጥእ ባርያህን እኔንም አስበኝ፡፡
  •         አቤቱ ሕዝብህን አድን ርስትህንም ባርክ፡፡ ጠብቃቸው እስከ ዘለዓለምም ከፍ ከፍ አድርጋቸው፡፡

No comments:

Post a Comment