·
በደመናት ግሩም ነው፤ ከሰማያትም ይልቅ
ከፍ ያለ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመንገዱ ሁሉ ምስጉን ነው፤ የአማልክት አምላክ ፍጹም አሸናፊ ነው፡፡
·
የሌለበት የለም፤ የታጣበትም ጊዜ የለም፤ በመለኮቱ
ግን ፈጽሞ የታየበት ጊዜ የለም፡፡ እርሱን ማየት የሚችል የለም፤ አነዋወሩም እንደምን እንደሆነ የሚያውቅ የለም፡፡
·
ሰማይና ምድር ከዓለማቸው ሁሉ ጋር፤ ባሕርና ወንዞች በውስጣቸውም ያሉ
ሁሉ እርሱን የሚያመሰግኑ፡፡ በጸጋው ሁሉ የተፈጠረ፣ በቸርነቱም ሁሉ የሚያድር፡፡ ይኸውም አንድ የሚሆን፣ የአንድ አባት፣ የጌታ
አባት፤ ከወለደው ጋራ እውነተኛ ብርሃን የሚሆን የመሢሕ አባት ነው፡፡
·
የአብን ከልጁ ጋር አነዋወሩን የወልድንም ከአባቱ
ጋራ አነዋወሩን እንናገራለን፡፡ ከፍጥረት ሁሉ በፊት ከሰማያትም መፈጠር በፊት ምድር ሳትፈጠር፡፡
·
ተራራዎችና ኮረብቶች ሳይቆሙ፣ የአየርም ርዝመት ሳይታይ፣ የነፋስ ኃይል
ሳይነፍስ፡፡
·
ብልጭልጭታም ሳይመላለስ፣ የመብረቅም ፍጥነት
ሳይታይ፣ ነጎድጓድም ሳይሰማ፣ ደመናትም ሳይዘረጉ፡፡
·
ከመላእክትም መፈጠር በፊት፣ ከሰማይ በታች፣ ከምድርም፣ ከሚጠራ ስም
ሁሉ በፊት፡፡
·
ማንም አስቦ አጥልቆም አነዋወሩን ማግኘት አይችልም፡፡
ምንም እስከ ሰማይ ቢወጣ ከአጋዕዝትም ዘንድ ቢያልፍ፡፡ ዓይንን የተሞሉ
ሁለንተናቸው ብርሃን የሚሆን፣ ከአንደበታቸው ነደ እሳት የሚመስል ቅዳሴ የሚወጣ አራቱ እንስሳንም ቢያገኝ፡፡ ዳግመኛም ወደ ምድር
ቢወርድ፣ ባሕርንና ነፋስን፣ እሳትንም አልፎ ቢሄድ፡፡ ዳግመኛም ከዚያ ወጥቶ በመመካትም ሆኖ፣ በሕሊናም በመዋኘት ቀኙንና ግራውን
ቢመረምር፡፡
·
አነዋወሩ እንዴት እንደሆነ ያውቅ ዘንድ በአብና በወልድ በመንፈስ ቅዱስም
መካከል ሊገባ አይችልም፡፡
·
አብ ልጁን ወለደው፣ በዚህ ጊዜ እንዲህ ባለ
ዘመንም ወለደው አይባልም፡፡
·
ከአብ መወለዱ አይታወቅም፣ ጭንቅ ነውና፡፡ አነዋወሩም አይታወቅም የተሠወረ
ነውና፡፡ ለአባቱ ቀኙ ነው፡፡ ክንዱ፣ ልጁ፣ ወዳጁም፣ እንደእርሱ የሚሆን የሚመስለው ነው፡፡
·
አብ ልጁን
ወለደው፡፡ እንደተቸገረ ሰው ያገለግለው ዘንድ ለሥራ ርዳታ በምክንያት የወለደው አይደለም፡፡ሰማይንና
ምድርን በፈጠረም ጊዜ የረዳው የለም፣ ከሃሊ ነውና፡፡
·
እንደ ሰው ደክሞት ያረፈ አይደለም፡፡ የእሳት
ሰይፍ ከአፉ ይወጣል እንጂ፡፡ የተናገረውን በዚያው ጊዜ ያደርጋል፤ ያሰበውም በቅፅበት ይሆንለታል፡፡ የሕሊናት ሕሊና ጥበበኛም ብልሃተኛም እርሱ ነው፡፡
·
እንደ እርሱ በቀመር የሚቀመጥ፣ መሠረትን የሚሠራ፣ መሠረትን ተሸክሞ በጠፈር የሚኖር ማን ነው? በውኃ ላይ ይመሠርታል፣ በጥቃቅን ይሠራል፣ በረቂቅ ይጠቀልላል፣ በአሸዋ ይወስናል፡፡ በነፋስ ያጸናል፣ ውኃውን ሰቅሎ
ሰማይ ይለዋል፡፡
·
ውኃን በማኅፀን ይቋጥራል፣ ሥጋም ይሆን ዘንድ ያረጋዋል፣ በስር ያስረዋል፣ በጅማትም
ያጸናዋል፣ ጠጉርን ይቆጥራል፡፡ ልብን ይመረምራል፣ ኩላሊትንም ያውቃል፡፡
·
አብ ልጁን
ወለደው፤ ዕለት ግን የለም፤ ሰዓትም የለም፡፡ በወለደውም
ጊዜ አባቱ ከርሱ ብቸኛ አልሆነም፤ መላእክትንም ለምስጋና ሳይፈጥር
ምስጋናው የተቋረጠ አይደለም፡፡ የአብ የወልድና
የመንፈስ ቅዱስ ምስጋና የመላ ነው እንጂ፡፡
·
አባታችንን አዳምን በፈጠረውም ጊዜ
መሬትንና ውኃን፣ ነፋስንና
እሳትን ያመጣ ዘንድ የተመላለሰ አይደለም፤ከዙፋኑ ሳይነቃነቅ ፈጽሞ ሳይነዋወጽም ነው እንጂ፡፡
·
በዚያም ሳለ
አራቱን ባሕርያት ነሳ፡፡ ሁለቱን ከሚዳሰስ፣ ሁለቱን ግን
ከማይዳሰስ፣ ሦስቱን ከሚታይ፣ አንዱን ከማይታይ፡፡
·
ቅዱሳት በሚሆኑ እጆቹ በራሱ አሳምሮ ፈጠረው፤ ሳመው፣ ወደደውም፡፡ የሕይወትንም መንፈስ በርሱ ላይ እፍ
አለ፡፡ አየራትንና
ሰማያትንም ሳይፈጥር የተዋረደ አይደለም፤ በዙፋን የጸና በመንግስትም የጸና ነው እንጂ፡፡
·
በላይ ላሉት
ድምፅን አሰማ፤ በታች ያሉትንም አንቀጠቀጠ፤ ደመናትንም ረገጠ፡፡ ያለ እሳት አቃጠለ፤ ያለ ውኃም አቀዘቀዘ፡፡
·
ፀሐይንና ጨረቃን በፈጠረም ጊዜ
እንደ ጨለመበት ሰው ሊያበሩለት አይደለም፤ ከርሱ ብርሃን የስንዴ ቅንጣት ያህል ጥቂት ሰጣቸው እንጂ፤ ስለዚህም በሰው ላይ አበሩ፡፡
·
እንግዲህ
የሚታየውንና የማይታየውን ፈጥሮ፤ አዝጋጅቶ ሰርቼ ፈጸምሁ፤ ካገኘኝም ድካም ሁሉ አርፋለሁ ብሎ የተመካ አይደለም፡፡ እርሱ ሳይደረግ አወቀ፣ ሳይሠራም ፈጸመ፤ ጻድቃንና ኀጥአንን፤ ክፉዎችንና
በጎዎችን ሳይፈጥር፡፡
·
ሰውን ሳይፈጥረው ገነትን አዘጋጀ
የወደደውን ወደ እርሷ ያገባ ዘንድ፤ የሲኦልንም እሳት አዘጋጀ የጠላውን ወደ እርሷ ያገባ ዘንድ፡፡
·
የመረጠው
ብፁዕ ነው፤ የወደደውም ብፁዕ ነው፡፡ እንግዲህ ይህን ቃል በፍጹም መጠንቀቅ
እናስተዉል፤ እሳትና ውኃ ወደ ተቀላቀለበት ከርሱም ዋኝቶ መውጣት ወደማይቻለን ታላቅ ባሕር እንዳንገባ፡፡
·
እኛስ የአብንና የወልድን የመንፈስ
ቅዱስንም ነገር እናስተውል ሐዋርያት እንዳስተማሩን፣ ለርሱ አንድ የሚሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ልጁ እንደሆነ አብ የልጁን ነገር ይናገራል ብለው፡፡ ወልድም የወለደው እግዚአብሔር አብ
እንደሆነ ይናገራል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ከአብ እንደወጣ (እንደ ሰረፀ) ከወልድም እንደ ነሣ ይናገራል፡፡
·
አንዲት ክብር፣ አንዲት ስልጣን፣ የማይለይ አንድ ኃይልም ነው፡፡ በባሕርዩ ዘንድ ምክንያት፣ መለየትም የለም፡፡ በመለኮቱም ዘንድ ጉድለትና ጭማሪ የለም፡፡
·
ጌታችን ለደቀመዛሙርቱ ያነዋወራቸውን
ነገር እንደ ነገራቸው፡፡ ተቀዳሚና ተከታይ፣ ቀኝና ግራ የለብንም ብሎ፡፡ጠፈር የለብንም፣ መሠረትም የለብንም፣ ጠፈርም
መሠረትም እኛ ነን፡፡
·
እኛን ማየት
የሚቻለው የለም፡፡ አነዋወራችንም እንደምን እንደሆነ የሚያውቅ የለም፡፡ እኛ ሁሉን
እናውቀዋለን፣ ሁሉንም እኛ እንረዳዋለን፡፡ የቀረበውን እናርቀዋለን፣ የራቀውን እናቀርበዋለን፡፡ እንደማይሰማ
የአንደበትን ጩከት ቸል እንላለን፤ የውሳጣዊን ልብ ለሆሳስ (ሹክሹክታ ) እናውቃለን፡፡
·
አባቴ እኔም መንፈስ ቅዱስም ደጅ
በርና ማደሪያ ነን ::
·
አባቴ እኔም
መንፈስ ቅዱስም ግርማና ጸጋ ሞገስም ነን ::
·
አባቴ እኔም መንፈስ ቅዱስም ፀሐይና
ብርሃን ዋዕይም ነን ::
·
አባቴ እኔም
መንፈስ ቅዱስም እሳትና ነበልባል ፍሕምም ነን ::
·
አነዋወራችን እንዲህ ነው ፍጻሜያችንም
እንዲህ ነው ዘመናችንም ለዓለም አይደለም ለዘለዓለም ዓለም ነው እንጂ፡፡ ዳግመኛ ቁጥርና ፍጻሜ የለውም፡፡
·
መዓቱ የራቀ
ምሕረቱም የበዛ ዕውነተኛ፤ የታገሰበት ጊዜ የለም ያልታገሰበትም ጊዜ የለም፡፡
·
የበደለውን ፈጽሞ ወደ እርሱ እስኪመለስ
ድረስ ይታገሳል፡፡
·
በተቆጣ ጊዜም
ኀጥአንን በጥፋት
ውኃ አጠፋ፡፡ ቃሉን የጠበቁ ስምንት ሰዎችንም አተረፈ፡፡ ከአባታቸውም
ጋራ ለዘለዓለም የሚሆን የእውነት ኪዳንን አጸና(አቆመ)፡፡ የአማልክት
አምላክ የሚያቃጥል እሳት የሚያድን እሳት፡፡
·
ስሙ ማነው? የልጁስ ስም ማነው? ብሔሩ እንደምን ያለ ነው? ሀገሩስ እንደምን ያለ ነው?
·
ዙፋኑ በእሳት
የተከበበ ነው ማደሪያውም በውኃ የተታታ ነው፡፡ በቤቱም ዙሪያ
ላይ የማይፈስ የውኃ መርገፍ አለ፤ ከዙፋኑም ብልጭልጭታ ይወጣል፤ ውስጡ እንደጋለ እሳት ነው፡፡ በውስጡ እንደ
ክረምት ቀስተ ደመና ያለ ደገኛ ብርሃን አለ፡፡ ዙሪያው መብረቅ ነው፡፡
·
ከዚያም መንበር አጠገብ ዐራቱ እንስሳ
ኅብሩ እንደ በረድ ነጭ የሆነ ሰፊ መንበር በራሳቸው እንደተሸከሙ ሆነው አሉ፡፡
·
በዚህም መንበር
ዙሪያ ሃያ አራት ካህናት፡፡ በፊታቸውም የበግዑን ሥዕል ደምን የተረጨች፣ ልብስንም፣ የታተመ መጽሐፍንም ያያሉ፡፡
·
ይህንም መንበር በዞሩ ቁጥር ለዚያ
ለበጉ ሥዕልና በደም ለታለለች ለዚያች ልብስ፣ ለታተመው
መጽሐፍም ፫ት ጊዜ ይሰግዳሉ፡፡ በአዳራሹም ድንኳን የምስጋና ጢስ ይመላል፡፡ ከዚህም መንበር በታች ጎዳናው ሁለት የሆነ ባሕር ይፈልቃል፡፡ የብርሃን ባህርና የነፋስ ባሕር፡፡
·
የአማልክት
አምላክ በዚያ የሚኖር አይደለም፡፡ የአጋዕዝትም ጌታ በዚያ የሚወሰን አይደለም፡፡ በውጭ ይኖራል
በውስጥም ይገኛል፡፡
·
ያገኙት ዘንድ አይሄዱም፡፡ በሹትም ጊዜ አይታጣም፡፡ በያዙትም ጊዜ አይዳሰስም ከኅሊና
ልዩ ነውና፡፡
·
ባለጸጋውን
ይጠብቃል ከድኃም ጋር ይኖራል፤ ትሑቱን ሰው
ይወዳል፣ ትዕቢተኛውን ግን ቸል ይላል፡፡ ቢፈቅድ ያጸድቃል
ቢወድም ያድናል፤ እንደማይሰማ ቸል ይላል፤ እንደማያይ
ዝም ይላል፤ እንደማያውቅ ይታገሳል፤እንደማይሰጥ ያዘገያል፡፡
·
የአማልክት አምላክ የአጋዕዝትም
ጌታ የጽኑዓን ጌታቸው መላእክትና ሊቃነ መላእክት የሚሰግዱለት እርሱ ነው፡፡
·
በማየት የሚሰግዱለት
አይደለም ለመንበሩ ይሰግዳሉ፤ ለጌትነቱም ይገዛሉ እንጂ፡፡ ፈቃዱን ሁሉ
ለመስራት ወደ አራቱ ማዕዘነ ዓለም ይወጣሉ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤል በትዕቢት ኃይል ያይደለ ጩኸው ቅዱስ
እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል የማይሞት ስለሰው ፍቅር የሞተ ቅዱስ ሕያው ይላሉ፡፡
·
በዓለም የሚወለዱ ነፍሳት ከአፉ
እስትንፋስ ከተገኘች ከአንዲት መዝገብ ይወጣሉ፤ ይለመልማሉም፡፡
·
በአንዲትም
መዝገብ ክርዳድ የሌለበት ስንዴ ይገባል፡፡ የጻድቃን ነፍሶቻቸው በዚያ ይኖራሉ በዚያም ይጠበቃሉ፡፡ለሁሉ እንደ ሥራው እስኪከፍለው ድረስ፤ ከዚያ ፍስሐ
ሐሴትም አለ፡፡ የሁሉ አባት አዳም ከዚያ አለ፡፡ የአበው አርእስቶች
አቤልና ሴት ሄኖስም ከፍሬያቸው ጋራ በዚያ አሉ፡፡
·
የጌታ ወዳጆች አብርሃምና ይስሐቅ
ያዕቆብም ከዚያ አሉ፤ ሙሴና አሮን ካህናት ከዚያ አሉ፡፡ ዳዊትና ሕዝቅያስ ኢዮስያስም፤ ሃይማኖታቸው የቀና ነገሥታትም ሁሉ፡፡ ነቢያት ከትንቢታቸው ጋራ ከዚያ
አሉ፡፡ መክፈቻዎች በእጆቻቸው የተያዙ የዋህድ ደቀ መዛሙርት ከዚያ አሉ፡፡ በበር ተቀምጠው የወደዱትን ወደ እርሷ ያገቡ ዘንድ፡፡
·
የጳጳሳት
አለቆች ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት ቀሳውስትና ዲያቆናት፤ ጌታቸው ያመናቸው፤ ሹመታቸውን የመለሱ ከዚያ አሉ፡፡
·
ሰማዕታት ዘውዳቸው ከፀሐይ ሰባት
እጅ እያበራ ከዚያ አሉ፡፡ ጻድቃን በትዕግስታቸው ከዚያ አሉ፡፡
·
ቁጥር የሌላቸው
የአብና የወልድ የመንፈስ ቅዱስም ሰራዊት ወንዶችም ሴቶችም ከዚያ አሉ፤ በፍጹም ደስታ በሐሴትም ከዚያ
ይኖራሉ፡፡ ከቀድሞው ይልቅ ዕፅፍ ርስታቸውን
እስኪቀበሉ ድረስ፡፡
·
ጻድቃን በክብር፤ የዋሃን
በክብር፤ የተመረጡትም በክብር ከዚያ ይኖራሉ፡፡ አቤቱ
የምትመልስ አንተን፤ የምትሰማ አንተን፤ የምትረዳ አንተን እንለምንሃለን ::
·
አቤቱ ከዚህ
ከሚያልፍ ዓለም ተለይተው ስለሞቱና ስለተሰደዱ የሞት ስልጣን ስለሰለጠነባቸውና ከመቃብር በታች ስለተከደኑ ሰዎች እንማልድሃለን፡፡
·
አቤቱ ሥጋን ከመንፈስ ጋራ አንድ አድርገህ
ስታስነሳ በክብር ወደ መነሳት ትጠራቸው ዘንድ እንለምንሃለን፤ እንማልድሃለን፡፡ ዓይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው
ልቡናም ያልታሰበውን በልጅህ በኢየሱስ ክርስቶስ ያዘጋጀኸውን በጎ ዋጋ እየሰጠህ ለዘለዓለሙ፡፡
No comments:
Post a Comment