Friday, April 29, 2016

ኢየሱስ የትንሣኤችን በኩር፤ የእረፍታችንም አስገኚዋ!

ፋሲካ የእብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም አለፈ የሚል ነው፡፡ በዘጸ 12 ላይ በዝርዝር እንደምናነበው ለበዓለ ፋሲካ መጀመር ምክንያቱ እስራኤል ከግብፅ የወጡበት ሁኔታ ነው፡፡ “ . . . እኔም በዚያች ሌሊት በግብፅ ገር አልፋለሁ በግብጽም አገር ከሰው እስከ እንስሳ ድረስ በኩርን ሁሉ እገድላለሁ፣ በግብፅም አማልክት ሁሉ ላይ እፈርድባቸዋለሁ፡፡ እኔ እግዚአብሔር ነኝ ፡፡ ደሙም ባላችሁበት ቤት ምልክት ይሆናችኋል፣ ደሙንም ባየሁ ጊዜ ከእናንተ አልፋለሁ፣ እኔም የግብፅን አገር በመታሁ ጊዜ መቅሰፍቱ ለጥፋት አይመጣባችሁም፡፡” ዘጸ 1212-13 ፡፡ እስራኤል የቤቶቻቸውን ጉበንና መቃን በፋሲካው ደም ከቀቡ በኋላ ቀሳፊው መልአክ ወደ ምድረ ግብፅ ወርዶ ከሰውና ከእንስሳት ወገን በኩር የሆነውን ሁሉ እየቀሰፈ ሲገድል የፋሲካው በግ ደም ምልክት የሆነባቸውን የእስራኤል ቤቶች ግን አልፏቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ እግዚአብሔር አምላክ ቃል ወደ ገባላቸው የእረፍት ምድር ከነዓን ሊገቡ እስራኤል ከግብጽ ምድር መውጣት የጀመሩት፡፡
በብሉይ ኪዳን የነበረው የፋሲካ በዓል ሥርዐት ዛሬ በሐዲስ ኪዳን ለሚከበረው የጌታችን በዓለ ትንሣኤ ምሳሌ ሲሆን በፋሲካው የሚታደረደው በግ ደምም ለጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቤዛነቱ ደም ምሳሌ ነው፡፡ ሕዝበ እስራኤል በምድረ ግብፅ ሲኖሩ አገዛዝ ጸንቶባቸው በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፡፡ እግዚአብሔርም ከአባቶቻቸው ጋር የገባውን ኪዳን አስቦ በብዙ ድንቅ ተአምራት ከግብፅ በማውጣት ለእረፍት ወደ አሰባት ከነዓን አግብቷቸዋል፡፡ በሥጋ የሆነው የእስራኤል ስደት ፣ መከራና ወደ እረፍት መመለስ በዘመነ ሥጋዌ በክርስቶስ ትንሣኤ ለሆነው የአዳም ድኅነትና ወደ መንግስቱ መመለሰ ምሳሌ ሆኗል፡፡ አዳም አታድርግ የተባለውን አድርጐ ከገነት በተሰደደና ለሞት የተገባ በሆነ ጊዜ የአጋንንት አገዛዝ ሰልጥኖበት ፣ ከእርፍት ርቆ በብዙ መጨነቅ በመከራ ውስጥ ሊኖር ግድ ሆኖበታል፡፡ ከዚህ ሁሉ በኋላ ነው እንግዲህ አዳምና ልጆቹ በክርስቶስ መሞት ሞት ተሸንፎ፣ ድል መንሳቱም ተወግዶ በትንሳኤው እንዲያርፉና የመንግስቱ ወራሾች እንዲሆኑ የተገባቸው፡፡ በዚህም የተነሳ በብሉይ ኪዳን ይከበር የነበረው የፋሲካ በዓል አሁን በዘመነ ሐዲስ ከምናከብረው በዓለ ትንሣኤ ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ሊሆን ችሏል፡፡ ምክንያቱም የፊተኛው በዓል ለኋለኛው ምሳሌውና ጥላው ሲሆን የኋለኛው ደግሞ እውነተኛውና አካሉ ስለሆነ ነው፡፡ የብሉይ በዓለ ፋሲካ በከነዓን ለሚሆነው እረፍት መነሻ እንደነበረ ሁሉ የሐዲስ ኪዳኑ በዓለ ትንሣኤም በክርስቶስ ቤዛነት በመንግቱ ለተሰራልን እረፍት መነሻ ነው፡፡ በአጠቃላይ እግዚአብሔር አምላክ በዓለ ፋሲካንም ሆነ በዓለ ትንሣኤን ያደረገልን ከእረፍት/ ከበዓለ ሃምሳ/ በፊት ነው፡፡ ምክንያቱም እነዚህ በዓላት ወደ እረፍቱ ለመግባት ልንጓዛቸው የሚገቡን ጉዞዎች ፣ ልናልፍባቸው የተሰሩልን ምዕራፎች እንዲሆኑ ፈቃዱ ሆኗልና፡፡
እረፍት፡- እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ልጅ ከፈጠረው በኋላ ያለ እረፍት እንዲኖር አልተወውም፡፡ በየእለት ኑሮው ውስጥ እረፍትን እየተለማመደ ኖሮ በመጨረሻ ለፍፃሜው ወደ ታሰበለት እውነተኛና የዘለዓለም እረፍት እንዲደርስ አድርጐታል ፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ፍጥረታትን ፈጥሮ ከጨረሰ በኋላ እንዳረፈ ከመጽሐፍ ቅዱስ እናነባለን፡፡ ዘፍ 21-2፡፡ እርሱ በባህሪው ድካም የሚስማማውና እረፍት የሚያሻው ሆኖ ሳይሆን ለሰው ልጆች ስለ እረፍት የሚኖረን መረዳት በስሜታዊነትና በችኮላ የሚደረግ እንዳይሆን፣ በብዙ ሂደትና በጥልቀት የተደረገ እንዲሆን ሲል እግዚአብሔር አምላክ እረፍትን በብዙ አይነትና መንገድ ሊያስተምረን ፈቃዱ ሆኗል፡፡
የመጀመሪያው እረፍት እንቅልፍ ነው፡፡ በዕለት ተግባራችን ስንደከምና ስንሰራ ውለን በእንቅልፍ እናርፋለን፡፡ ከእንቅልፋችን በኋላ ግን ከድካማችን ታድሰንና በርትተን ለአዲስ ጥንካሬ፣ ለሌላ አዲስ ቀንና ኑሮ እንዘጋጃለን፡፡ ይህ እንግዲህ እኛ አስበን ያገኘነውና ተመራምረን የደረስንበት ሳይሆን እግዚአብሔር በተፈጥሯችን ውስጥ የሰራልን ሕግ ነው፡፡ በመሆኑም እንዲህ በየዕለቱ በእንቅልፍ እያሳረፈን በመንግስቱ ያሰበልንን ከሁሉ የሚሻልና የሚበልጥ እረፍት እንድናስብና ተስፋ እንድናደርግ ያለማምደናል፡፡
ሰንበት፡- ሌላኛው የተሠራልን እረፍት ደግሞ የሰንበት እረፍት ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረታትን የመፍጠር ስራውን ሰርቶ ከፈጸመ በኋላ በሰባተኛው ቀን ከሰራው ሥራ ሁሉ አርፏል፤ ሥራውን የፈጸመባትንም ዕለት ለሰው ልጆች ሁሉ የእረፍት ቀን እንድትሆንና ሰው ሁሉ ከተግባረ ሥጋ እንዲያርፍባት ሥርዐትን ሰርቷል፡፡ “ሰባተኛው ቀን ለእግዚአብሔር አምላክ ሰንበት ነው፡፡ አንተም እንደምታደርፍ ሎሌህና ገረድህ ያርፉ ዘንድ፣ አንተ፣ ወንድ ልጅህም፣ ሴት ልጅህም፣ ሎሌህም፣ ገረድህም፣ በሬህም፣ አህያህም፣ ከብትህም ሁሉ፣ በደጆችህም ውስጥ ያለ እንግዳ በእርሱ ምንም ሥራ አትሥሩ” ሲል በዓል በማክበር ጻድቃን ባለማክበርም ደግሞ ኀጥአን የማይባሉ እንስሳትና ምድሪቱም ጭምር በሰንበት እረፍትን እንዲያደርጉ ሥርዐት ተሰርቷል፡፡ ዘዳ 514 ፤ ዘጸ 231ዐ፡፡
ከነዓን፡- ስለ እረፍት ሲነሳ ሌላው የሚነሳው ዐቢይ ጉዳይ ደግሞ እግዚአብሔር ለእስራኤል በከነዓን የሠራላቸው እረፍት ነው፡፡ ከ4ዐዐ ዓመታት በላይ የግብፅ መከራና ድካም በኋላ ሙሴን አስነስቶ ሕዝቡን ከፈርኦን እጅ ሊያድን እንዳሰበና ከነዓንንም የእረፍት ምድር አድርጐ ሊያወርሳቸው እንደሆነ ነግሮታል፡፡ ከዚህም በኋላ በብዙ ድንቅና ተአምራት ከግብፅ አውጥቶና በመንገዳቸው ሁሉ ውስጥ ድልን ሰጥቶ ለእረፍት ወደ አሰበላቸው ምድር ወደ ከነዓን አግብቷቸዋል፡፡
ሰንበተ ክርስቲያን፡- ሰንበተ ክርስቲያን የምትባለው ዕለተ እሁድ ናት፡፡ ይህቺ ቀን ጌታችን ሰው ይሆንባት ዘንድ በማህፀነ ማርያም ያደረባት፣ የማዳን ሥራውን ፈጽሞ፣ ሞትና መቃብርን ድል ነስቶ የተነሳባት ዕለት ናት፡፡ እሁድ እግዚአብሔር ፍጥረትን መፍጠር የጀመረባት ስትሆን ወደፊትም ዓለምን በማሳለፍ የዚህች ዓለም የህልም ኑሮ የሚፈጸምባት ዕለት ናት፡፡ ከዚህም የተነሳ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ይህችን ዕለት ለይቶ “የጌታ ቀን” ብሏታል:: ራዕ 18 ፡፡ የጌታ ቀን ማለቱ ሌሎቹ የጌታ ስላልሆኑ ሳይሆን ደገኛና የተለየ ሥራ የተሰራባት ቀን ስለሆነች ነው፡፡ ስለዚህም የጌታችን ጽንሰቱን፣ ሥጋዌውን፣ ትንሣኤውን፣ ለሐዋርያትም መንፈስ ቅዱስን የላከበትንና ዳግም ምጽአቱን በዕለተ እሁድ መሆናቸውንና መደረጋቸውን በማሰብ የምትከበር ታላቅ የክርስቲያኖች በዓል ልትሆን ችላለች፡፡
ሰንበት ጥንተ እረፍት ናት፤ በመጀመሪያ እግዚአብሔር አርፎባታልና፡፡ የእረፍት ጥንት መባሏም ተከታይ ስላላት ነው፡፡ ሰንበት ወደፊት ለሚመጡት እረፍቶች አብነትና ጥላ እንጂ ፍጻሜ አይደለችም፡፡ በሌላም በኩል ጥንት የሌለው ፍፃሜ እንደሌለ ሁሉ ሰንበት የፍጻሜው ምሳሌና ማሳያ እንጂ በራሷ የመጨረሻው እረፍት ወይም ተፍጻሜተ እረፍት አይደለችም፡፡ እግዚአብሔር እስራኤልን በተደጋጋሚ ሰንበታቴን አትናቁ የሚላቸው ወደፊት ሌላ የሚያወርሳቸው መካነ እረፍት ስላለውና ለዚያ ይበቁም ዘንድ በመጀመሪያ ሰንበትን ማክበር ይጠበቅባቸው ስለነበረ ነው፡፡ ዘሌ 1930262፡፡ በዚህም የተነሳ አባቶቻችንን ከሰንበተ አይሁድ/ቀዳሚት ሰንበት አንስቶ ስለ እረፍት እያስተማራቸው ወደ ከነዓን እረፍት አደረሳቸው ፡፡ ይህም የከነዓን እረፍት ለሥጋ የሆነ እንጂ እረፍተ ነፍስ የለበትምና በሂደት የነፍስ እረፍት ወደተገኘባት የሐዲስ ኪዳን ሰንበት ደረስን፡፡ ይሁን እንጂ የሐዲስ ኪዳኗ ሰንበትም ብትሆን እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሰራት ፍፃሜ አይደለችም፤ እንኪያስ ለመጨረሻው እረፍት የቀረበችና የዘለዓሙን እረፍት የምንማርባትና የምንለማመድባት የመንግስቱ አንፃር ናት እንጂ፡፡
መንግሥተ ሰማያት፡- እግዚአብሔር በአንፃረ ሰንበት ከነዓንን እንዳስታወቀን፤ በአንፃረ ከነዓን ደግሞ ሰንበተ ክርስቲያንን አስታውቆናል፡፡ ይህ ሁሉ ግን ወደ ፍጻሜው የተደረገ ጉዞ እንጂ ፍፃሜው አልነበረም፡፡ ስለሆነም ከዚህ በፊት በነበሩትና በሂደት ቀስ በቀስ ባስተማረንና ባሳየን እረፍት እንፃር መንግሥት ሰማያት የመጨረሻዋ መካነ እረፍታችን እንደሆነች አስተማረን፡፡ በዚህም የተነሳ መንግሥተ ሰማያትን እረፍቴ ሲል ጠራት፡፡ “ሥራው ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ምንም እንኳ ቢፈጸም እንግዲህ ወደ እረፍቴ አይገቡም ብዬ በቁጣዬ ማልሁ እንዳለ እኛስ ያመንን ወደ እረፍቱ እንገባለን ” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ከከነዓን የምትበልጥና የምትሻል መካነ እረፍት እንዳለችን ነገረን፤ ይህቺውም ደግሞ መንግሥተ ሰማያት ናት፡፡ ዕብ 43፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ቅዱስ ጳውሎስ ዝቅ ብሎ እንዲህ ጽፎልናል፡- “እንግዲያስ የሰንበት እረፍት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ቀርቶላቸዋል፡፡ ወደ እረፍቱ የገባ፤ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ እርሱ ደግሞ ከሥራው አርፏልና፡፡” ዕብ 49-10፡፡ እግዚአብሔር አረፈ ሲባል ሥራውን/መፍጠሩን ፈጽሞ ባለማለፍ ለዘላለም ጸንታ በምትኖር መንግስቱ አለ ማለት እንደሆነ ሁሉ፤ በእርሱ ያመንን ክርስያኖችም እግዚአብሔር አምላካችን በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ የሰራልን የመንግስተ ሰማት እረፍት ባለማለፍ ለዘለዓለም ጸንታ የምትኖር መካነ እረፍት ናት፡፡ በመንግስቱም ደግሞ እስከ ሞት ከወደደን ከአምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ደስ እያለን ጸንተን እንኖራለን፡፡
ትንሣኤና እረፍት
የጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ከእረፍታችን ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው፡፡ ለምን ቢሉ የጌታችን ትንሣኤ ለእረፍታችን መነሻና ጅማሬ ስለሆነ ነው፡፡ እረፍት የምንለው ያለድካምና ያለመሞት ለዘለዓለም በሕይወት መኖርን ነው፡፡ ይህ እንዲሆን ደግሞ ሞት የግድ መሸነፍ ነበረበት፡፡ ሞት ከአዳም ጀምሮ እስከ ክርስቶስ ስጋዌ/መገለጥ ድረስ ሰዎችን ሁሉ ሥጋቸውን ወደ መቃብር፣ ነፍሳቸውን ደግሞ ወደ ሲኦል በማውረድ አስቀድሞ ወደታሰበልንና ወደ ተሰራልን የመንግስቱ እረፍት እንዳንገባ እንቅፋት ሆኖ ቆይቷል፡፡ ሞት እያለ ደግሞ ወደ እረፍታችን መካን ልንደርስ ስለማንችል ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦና በሥጋው የእኛን ሞት ሞቶ ብዙዎችን ሲያሸንፍ የነበረውን አሸናፊ በማሸነፍ በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ከሞት በክብር ትንሣኤ ተነስቷል፡፡ ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ በክርስቶስ ትንሣኤ የምናምን ምእመናን የትንሣኤያችን በኩር በሆነው በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና በማዳኑ በኩል ለእረፍታችን ወደ ሰራልን መንግስቱ መግባት ቻልን፡፡ በዚህም የተነሳ ክርስትናችን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ላይ የተመሠረተ ሆኗል፡፡ ሞቱ የኀጢአት ሥርየት አግኝተን ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅንበት እንደሆነ ሁሉ፤ ትንሣኤውም ደግሞ እምነታችንና ተስፋችን ፍጹም እውነት መሆኑን የምንመሰክርበትና ወደ ዘለዓለም እረፍታችን የምንደርስበት መንገዳችን ሆኗል፡፡ ክርስቶስ የሙታን ሁሉ በኩር መባሉ ከእርሱ በፊት ሞትን አሸንፎ በገዛ ሥልጣኑ የተነሣ ስለሌለና በእግዚአብሔር ተአምራት የተነሡትም ሁሉ እንደገና ተመልሰው ወደ መቃብር ስለወረዱ ብቻ ሳይሆን ከከርስቶስ መነሳት በኋላ በክርስቶስ የሚያምኑ ሁሉ የክርስቶስ ትንሣኤ ተካፋዮች ስለሚሆኑና ከእርሱ የተነሳ ከሞት የሚነሱ በመሆናቸውም ጭምር ነው፡፡
የክርስቶስን ትንሣኤ በዓል ስናከብር የተለየ የአምልኮ ሥርዐትን የምንከተልበት የራሱ የሆነ ትልቅ ምሥጢር አለው፡፡ ይኸውም ማለፍ የሌለበት የዘለዓለም እረፍታችን መነሻው የክርስቶስ ትንሣኤ ከመሆኑ የተነሳ ከሞት በኋላ የምንቀበለውን እረፍት በምድር ላይ ሆነን እንድንገነዘበው፣ እንድንናፍቀውና እንድንለማመደውም በሰሙነ ትንሣኤ የተሠሩልን የቤተ ክርስቲን ሥርዐቶች የጎላ ድርሻ አላቸው፡፡ ከትንሣኤው በፊት ባሉት ሃምሳ አምስት ቀናት ውስጥ በጾም ከመቆየታችን በተጨማሪ በጾሙ ውስጥ ያሉት ስምንቱም ሳምንታት የየራሳቸው ስያሜ ኖሯቸው ለየእንዳንዳቸው የተለየ ንባብና መዝሙር እንዲኖራቸው ተደርጓል፡፡እነዚህም ንባባትና መዝሙራት ነገረ ክርስቶስንና የመድኃኒታችንን ትምህርቶች የሚያወሱ ሆነው በሂደት በጾሙ መጨረሻ ላይ ወዳለው የክርስቶስን ህማምና ሞት፣ ስለ ሰዎች ፍቅር የተቀበላቸውን መከራዎች ሁሉ ወደምናስብበት ሰሙነ ህማማት የሚያደረሱን ከዚያም በመንፈሳዊ ተመስጦና ልዕልና ልናከብረው ወደሚገባን የትንሣኤው በዓል እንዲያደርሱን ሆነው የተሰሩ ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ የእረፍታችን መጀመሪያ የሆነውን የክርስቶስን ትንሣኤ ከማክበራችን በፊት ሥጋችንና ነፍሳችንን በማዘጋጀት በልዩ መንፈሳዊነት፣ በጠለቀ መረዳትና ተመስጦ ሆነን፤ በሰማያት ካሉ ቅዱሳኑና እነርሱንም ካከበረ ከመድኃኒታችን ህብረት ውስጥ ሆነን ልናከብር ስለሚገባን በምድርም ያለው ሥርዐት መንፈሳዊ ሆኖ ተሰርቶልናል፡፡ በሁሉም የጾሙ ሳምንታት በተለይም ደግሞ በሰሙነ ህማማት ወስጥ የምንደርስበት ከፍ ያለ መንፈሳዊነትና ተመስጦ ነገረ ትንሣኤውን በጥልቀት እንድንረዳውና ከጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መንፈሳዊ ህብረትና አንድነት እንዲኖረን ያግዙናል፡፡ ስለትንሣኤው ስንረዳ ደግሞ በትንሣኤው የሆነልንንና የተሠራልንን እረፍት እናስባለን፡፡ ይህንን ማድረግ ስንችል ብቻ በምድር ላይ ሆነን ትንሣኤውን እያከበርን ከመንፈሳዊው ዓለምና ከሰማያዊው ህብረት ጋር አንድ መሆንና መተባበር እንችላለን፤ በክርስቶስ ትንሣኤ ያገኘነውን መጻኢ እረፍትና የክብሩንም መንግስት አጥብቀን እንናፍቃለን፡፡ በጾማችንና በሌሎችም መንፈሳዊ ተግባሮቻችን የተሰሩልን ሥርዐቶች ሁሉ ዋናኛ ዓላማቸው እኛን ወደተሻለው መንፈሳዊ መረዳትና ከፍታ ማድረስ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ስለ ሕግ ሳይሆን ስለመንፈሳዊነትና ከፍ ስላለው የእግዚአብሔር እውቀትና መረዳት ስንል የተሰሩልንን መንፈሳዊ ሥርዐቶች አንፈጽማለን፡፡
ከጌታችን ትንሣኤ ጋር በተያያዘ አብረን የምናስበው ሌላው ዐቢይ ጉዳይ ደግሞ እስከ በዓለ ጰራቅሊጦስ ድረስ ያሉት ሃምሳ ቀናት ናቸው፡፡ እነዚህ ቀናት በጾሙ ውስጥ በነበሩት ሃምሳ አምስት ቀናት ሁሉ ውስጥ ስናስበው የነበረው የአዳም በደልና ያስከተለው ክፉ ውጤቱ ከእረፍትና ከጽድቅ ስላራቀን ወደ እረፍታችን የሚመልሰንን መድኃኒት ስንናፍቅ የነበረበት የአሮጌው ኪዳን ምሳሌ ናቸው፡፡ ከትንሣኤው በኋላ ያሉት ሃምሳ ቀናት ግን ወደ እረፍታችን ሊመልሰን ስለእኛ የደከመውን፤ ስለመተላለፋችን የተቀጣልንን፤ በሕይወት ስለመኖራችን የእኛን ሞት ሞቶ የእርሱን ሕይወት የሰጠንን ጌታችንንና መድኃኒታችን ኢሱስ ክርስቶስንና እርሱም ደግሞ በትንሣኤው የሰራልንን ዘለዓለማዊ እረፍት የምናስብባቸው ቀናት ናቸው፡፡ በእነዚህ ሃምሳ ቀናት ሁሉ ልክ እንደ አንዲት ቀን አድርገን ትንሣኤውን አንድናስብና ከክርስቶስ ጋር ህብረት አንድናደርግ ይፈለግብናል፡፡ የስርዓቱ ዋነኛ ዓላማም ይህ መንፈሳዊነትና በመንፈስ የሆነ መረዳት ነው፡፡ በምድር ላይ የጀመርነው እረፍትና መንፈሳዊ ህብረት ከክርስቶስ ሞት የተነሳ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም ከክርስቶስና ደስ ከተሰኘባቸው ቅዱሳኑ ጋር በምናደርገው አንድነትና ህብረት ፍጻሜውን ያገኛል፡፡
እረፍትን የሠራልንና ስለ እረፍትም ያስተማረን መምህራችን ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ እረፍታችንንም የሰራልን እርሱ ባወቀና በወደደ እንጂ ከእኛ በሆነው ጥረትና ትጋት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እረፍትን ያደረገልን ከአዳም በደል በኋላ ሳይሆን ገና ከጥንተ ፍጥረት ጀምሮ እርሱ ራሱ እግዚአብሔር ከስራው በማረፍ ለፍጥረቱ ሁሉ የሚሆን ሥርዐትን በመስራት ነው፡፡ ይህም የሆነው የባህሪያችንን ድካም የሚያውቅ እግዚአብሔር እርሱ ባወቀ በራሱ ምክርና ጥበብ ከድካማችን እንድንታደስና እንድንበረታ ያደረገበት መንገዱ ሲሆን በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ ያሰበልንንና ያዘጋጀልንን፣ እርሱ እንደወደደ መጠን የሰራልንን የምንማርበት ትምህርት ቤትና የምናጣጥምበት ዐረቦን እንዲሆን መውደዱ ዋነኛው ምክንያት ነው፡፡ በዚህም የተነሳ የጌታችንን ትንሣኤ ስናከብር ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል የጻፈልንን ቃል እናስባለን፡- ነገር ግን ወደ ጽዮን ተራራና ወደ ሕያው እግዚአብሔር ከተማ ደርሳችኋል፤ ወደ ሰማያዊቷም ኢየሩሳሌም፣ በደስታም ወደተሰበሰቡት ወደ አእላፋት መላእክት፣ በሰማያትም ወደተጻፉ (በአምላክ ልብ ወደታወቁት) ወደ በኩራት ማኅበር (በኩር በተባለ ጌታ አምነው ወደ ገቡት ከአቤል አንስቶ እስከ ምጽአት ድረስ ወደሚነሱት የጻድቃን ማኅበር)፣ የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር፣ ፍጹማንም ወደሆኑት ወደ ጻድቃን መንፈሶች፣ የሐዲስ ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፣ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል፡፡ ዕብ 1218-29፡፡
መልካም የትንሣኤ በዓልና በመንፈሳዊነት የሚደረግ በዓለ ሃምሳ ይሁልን!
የደብረ ሲና ደ/ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሰንበት ትምህርት ቤት፡፡



No comments:

Post a Comment